የሀገር ውስጥ ዜና

በትግራይ ክልል የሚገኙ የደም ባንኮችን ዳግም ወደ ሥራ ለመመለስ እየተሠራ ነው

By ዮሐንስ ደርበው

February 06, 2023

አዲስ አበባ፣ ጥር 29፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ ደም እና ቲሹ ባንክ አገልግሎት በትግራይ ክልል የሚገኙ የደም ባንኮችን ዳግም ወደ ሥራ ለመመለስ እየሠራ መሆኑን ገለጸ፡፡

የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሀብታሙ ታዬ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደተናገሩት÷ የሰላም ስምምነቱን ተከትሎ በትግራይ ክልል ከሚገኙ የደም ባንኮች መካከል የአክሱም ደም ባንክን ዳግም ሥራ ለማስጀመር የባለሙያ ቡድን ተልኮ የዳሰሳ ጥናት ሠርቷል፡፡

በአክሱም የደም ባንክ በኩል ደም ማሰባሰቡ በተደራጀ ሁኔታ እስከሚጀመር ድረስም በሁለት ዙር 400 ዩኒት ደም መላኩን ነው ያረጋገጡት፡፡

እንዲሁም ለመቀሌ ደም ባንክ 200 ዩኒት ደም መላኩን ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም የደም መቅጃ ከረጢት፣ የደም መመርመሪያ ሪኤጀንቶችንና ተያያዥ የሎጂስቲክ ድጋፍ መደረጉን ነው የገለጹት፡፡

ተቋማቱ በበቂ ዝግጅት ወደ ሥራ እንዲገቡ የአቅም ግንባታ እና የባለሙያ ቡድን በአካል ተገኝቶ ድጋፍ እንዲያደርግ ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡

ከላይ የተጠቀሰውን ድጋፍ ለማስቀጠል ብሎም በየአካባቢው ያለውን የደም ሕክምና ተጠቃሚዎች ፍላጎት ለማሟላት÷ በጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች ደም በመለገስ የሌሎችን ሕይወት የማቆየት ሥራ ይጠበቅባቸዋል ነው ያሉት፡፡

በዮሐንስ ደርበው

#Ethiopia

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!