ዓለምአቀፋዊ ዜና

ቱርክ ዛሬም በሌላ የመሬት መንቀጥቀጥ ተመታች

By Alemayehu Geremew

February 07, 2023

አዲስ አበባ፣ ጥር 30፣ 2015(ኤፍ ቢ ሲ) ቱርክ ዛሬም በሬክተር ስኬል 5 ነጥብ 7 ሆኖ በተመዘገበ ሌላ የመሬት መንቀጥቀጥ ተመታች።

የዛሬ ጠዋቱ አደጋ በሀገሪቷ ምሥራቃዊ ክፍል የደረሰ ነው ተብሏል፡፡

በሰሞኑ ቱርክና ሶሪያ ላይ የደረሱ አደጋዎች እስካሁን ከ5 ሺህ በላይ ሰዎች ሕይወታቸውን እንዳጡ የዜና ምንጮች አመላክተዋል፡፡

5 ሺህ 775 ኅንጻዎች ፣ ሆስፒታሎች እና መኖሪያ ቤቶች ደግሞ ተደርምሰዋል ነው የተባለው፡፡

በተጨማሪም አሰቃቂው አደጋ በርካታ ኅንፃዎችን አውድሞ በርካታ ነዋሪዎች ለክረምቱ ብርድና ቁር ማጋለጡን ሜትሮ ኒውስ ዘግቧል፡፡

ይህን ተከትሎ ከ300 ሺህ በላይ ብርድ ልብሶች በ41 ሺህ ጊዜያዊ መጠለያ ድንኳኖች መከፋፈላቸው ተጠቁሟል፡፡

ከ65 ሀገራት 2 ሺህ 600 የሚደርሱ የዕርዳታ ሠራተኞች የሀገሪቷን የነፍሥ-አድን አባላት ለማገዝ ቱርክ መድረሳቸው ተመላክቷል፡፡

ሆኖም ርዕደ-መሬቱን ተከትሎ ኅንፃዎቹ የተደረመሱበት ሁኔታ የነፍሥ ማዳን እና አስከሬን የመፈለጉን ሥራውን አስቸጋሪ አድርጎታል ተብሏል፡፡

ከሠዓታት በፊት የተከሰተው የመሬት መንቀጥቀጥ በርዕደ – መሬት መለኪያ 7 ነጥብ 8 ሆኖ የተመዘገበ ነበር፡፡