የሀገር ውስጥ ዜና

በ1 ነጥብ 4ቢሊየን ብር የሚገነባው የኮማንዶና አየር ወለድ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ ኅንፃ ግንባታ የመሰረተ ድንጋይ ተቀመጠ

By Alemayehu Geremew

February 07, 2023

አዲስ አበባ፣ ጥር 30፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በ1 ነጥብ 4ቢሊየን ብር የሚገነባው የኮማንዶ እና አየር ወለድ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ ኅንፃ ግንባታ የመሰረተ ድንጋይ ተቀምጧል፡፡

ኅንፃው በ400 ቀናት ዉስጥ እንደሚጠናቀቅ የተገለጸ ሲሆን ፥ በዛሬዉ ዕለት የመሰረት ድንጋይ የማስቀመጥና የስምምነት ፊርማ ሥነ-ሥርዓትም ተከናዉኗል፡፡

በመርሐ-ግብሩ ላይ የመከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ ÷ ኅንፃው ዘመናዊና ሁለገብ ሰራዊት ለመገንባት የተጀመሩ ስራዎች አንዱ አካል የሆነ ግዙፍ ፕሮጀክት ነው ብለዋል።

የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል ደስታ አብቼ በበኩላቸው ÷ ግንባታዉ ሦስት ዘመናዊ ባለ አራት ፎቅ ኅንፃን ጨምሮ የአንድ ሻለቃ ጦር መኖሪያ ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል።

ፕሮጀክቱን የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን በተቋራጭነት ይገነባዋል፡፡

የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ ዲዛይን እና ቁጥጥር ደግሞ እንደሚቆጣጠረው ከመከላከያ ሰራዊት ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

በመርሐ-ግብሩ የመከላከያ ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ማርታ ሉዊጂ ፣ ምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል አበባው ታደሰን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የሰራዊቱ አመራሮችም ተገኝተዋል።