የሀገር ውስጥ ዜና

ከ377 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ የአወዳይ ተለዋጭ የመንገድ ግንባታ ተጀመረ

By Alemayehu Geremew

March 01, 2023

አዲስ አበባ፣ የካቲት 22፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ከ377 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ የአወዳይ ከተማ ተለዋጭ የመንገድ ሥራ ተጀመረ፡፡

ተለዋጭ የመንገድ ሥራው 2 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የአስፋልት መንገድ የሚሸፍን መሆኑ ተመላክቷል፡፡

ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን የምትገኘውን እና ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴ የሚካሄድባትን የአወዳይ ከተማ የትራፊክ መጨናነቅ ይቀርፋል ተብሎም ተሥፋ ተጥሎበታል፡፡

የምስራቅ ሐረርጌ ዞን አስተዳዳሪ ወ/ሮ ሚስኪ መሐመድ ÷ የመንገዱ ግንባታ ከውስጥ በተሰበሰበ ገቢ የሚከወን መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

የመንገድ ሥራው በተያዘለት ጊዜ ተጠናቆ አገልግሎት እንዲጀምር የከተማው ሕዝብ አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርግም ጠይቀዋል፡፡

በተመሳሳይ ሌሎች የልማት ጥያቄዎች በቅደም ተከተል እንደሚመለሱም ነው ያረጋገጡት።

የአውዳይ ከተማ ከንቲባ አቶ ዲኖ አሚን በበኩላቸው ÷ ባለፉት ሁለት ዓመታት እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎች የብልፅግና ማሳያ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡

የአስፋልት ሥራው የ15 ሜትር የጎን ሥፋት ያለው እና በሁለት አቅጣጫ አራት ተሸከርካሪዎችን ማሳለፍ እንዲችል ሆኖ እንዲገነባ ውል የተቆረጠለት ፕሮጀክት ነውም ብለዋል፡፡

ፕሮጀክቱ በ15 ወራት ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በተሾመ ኃይሉ