የሀገር ውስጥ ዜና

በአዲስ አበባ በ217 አልሚዎች ላይ የማስተካከያ እርምጃ መወሰዱ ተገለጸ

By ዮሐንስ ደርበው

March 09, 2023

አዲስ አበባ፣ የካቲት 30፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን በተጠናቀቀው ስድስት ወር በመዲናዋ በ217 አልሚዎች ላይ የተለያየ የማስተካከያ እርምጃ መወሰዱን ገለጸ፡፡

የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ገዛኸኝ ሚዴሳ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንዳሉት÷ ማንኛውም ሕንጻ ከመገንባቱ በፊት ማሟላት ያለበትን አስገዳጅ ሁኔታ እንዲያሟላ ተገቢው ክትትል ይደረጋል፡፡

ግንባታዎች ለአካል ጉዳተኞች ምቹ መሆናቸውን ጨምሮ በወሰዱት ፕላን እና ዲዛይን መሰረት መገንባታቸውን እንዲሁም ለተፈቀደላቸው አገልግሎት መዋላቸውን የመከታተልና የማረጋገጥ ሥራ ይከናወናል ብለዋል፡፡

በባለስልጣኑ የግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ዳይሬክተር ኢንጂነር ከማል ጀማል÷ በተጠናቀቀው ግማሽ ዓመት ከማዕከል ጀምሮ እስከ ወረዳ ድረስ 217 ሕግ ተላልፈው በተገኙ አልሚዎች ላይ የተለያዩ እርምጃዎች መወሰዳቸውን ጠቁመዋል፡፡

እርምጃዎቹም የ350 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣትን ጨምሮ ከማስጠንቀቂያ እስከ ስራ ፈቃድ ስረዛ የደረሱ መሆናቸውን አስረድተዋል።

እርምጃዎቹን ተከትሎም አልሚዎች ማስተካከያ ማድረጋቸውን ነው ኢንጂነር ከማል ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት የተናገሩት፡፡

የሕንጻ መጠቀሚያ አገልግሎት የሚሰጠውም አስገዳጅ ሁኔታዎች መካተታቸው ሲረጋገጥ መሆኑ ተገልጿል፡፡

በዮሐንስ ደርበው

#Ethiopia

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!