የሀገር ውስጥ ዜና

በወንጀል ተጠርጥረው ክስ ቀርቦባቸው የነበሩ የህወሓት ወታደራዊና ሲቪል አመራሮች ክስ ተቋረጠ

By Melaku Gedif

March 30, 2023

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 21፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በወንጀል ተጠርጥረው ክስ ቀርቦባቸው የነበሩ የህወሓት ወታደራዊና ሲቪል አመራሮች ክስ መቋረጡን የፍትህ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡

በፌዴራል መንግስት እና በህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) መካከል በተፈረመው የሰላም ስምምነት መሰረት ከግጭቱ ጋር ተያያዥ የሆኑ ወንጀሎች ተጠያቂነት በተመለከተ ያለውን ዓለም አቀፍ ተሞክሮ ታሳቢ ባደረገ መልኩ በሽግግር ፍትህ ማዕቀፍ ሊታዩ እንደሚገባ ስምምነት ላይ መደረሱ ተገልጿል።

ስለሆነም በወንጀል ተጠርጥረው ክስ ቀርቦባቸው የነበሩ የህዝባዊ ወያነ ሃርነት ትግራይ ሲቪል እና ወታደራዊ አመራሮችን ክስ በማቋረጥ ጉዳያቸው በቀጣይ በሽግግር ፍትህ ማዕቀፍ እንዲታይ ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱ ተጠቁሟል፡፡

ስለዚህ በተገለፀው አግባብ ከዚህ ጋር በተያያዘ ክስ ቀርቦባቸው በክርክር ሂደት ላይ ይገኙ የነበሩ የወንጀል ክሶች በአዋጅ 943/2008 አንቀጽ 6 (3) (ሠ) መሰረት የተነሱ መሆኑን የፍትህ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል።