Fana: At a Speed of Life!

ወርቅን ከብሔራዊ ባንክ ዋጋ በላይ በሚገዙ አካላት ላይ ሕጋዊ እርምጃ ይወሰዳል – አቶ አሻድሊ ሀሰን

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 23፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወርቅን ከብሔራዊ ባንክ ዋጋ በላይ በሚገዙ ሕገ-ወጥ አካላት ላይ ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድ የክልሉ ርዕሰ-መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ገለጹ።

በርዕሰ-መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን የተመራ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ልዑክ በክልሉ መንጌ ወረዳ ወርቅ የሚመረትባቸውን አካባቢዎች የጎበኘ ሲሆን÷ የቀጣይ አቅጣጫም አስቀምጧል።

አቶ አሻድሊ ሀሰን በዚሁ ወቅት ÷ በክልሉ ከዚህ ቀደም የተሻለ የወርቅ ምርት ወደ ብሔራዊ ባንክ ይገባ እንደነበር አስታውሰው አሁን ሕገ-ወጥ የወርቅ አዘዋዋሪዎች በመበራከታቸው ወደ ብሔራዊ ባንክ የሚገባው ምርት ቀንሷል ብለዋል።

መንግስት ወርቅን በሕገ-ወጥ መንገድ ከብሔራዊ ባንክ ዋጋ በላይ በሚገዙ ግለሰቦች፣ ማኅበራት፣ ምርት በሚደብቁ አምራቾች እና ሌሎች ሕገ-ወጥ አካላት ላይ የተጠናከረ ሕጋዊ እርምጃ ይወሰዳልም ነው ያሉት፡፡

በጉብኝቱ ላይ የተገኙት የ22ኛ ክፍለ-ጦር ዋና አዛዥ ሌ/ጀኔራል ሠይፈ አንጌ በበኩላቸው÷በሕገ-ወጥ የወርቅ አዘዋዋሪዎች ላይ ጠንካራ ክትትልና ቁጥጥር እንደሚደረግ ተናግረዋል።

ሕገ-ወጥ የወርቅ ዝውውርን ለመቆጣጠር በቀጣይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት በማድረግ ዘመቻ ይካሄዳል ማለታቸውን ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.