የሀገር ውስጥ ዜና

የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት ሕብረተሰቡ ከግብይት መጭበርበር ሊጠነቀቅ እንደሚገባ አስገነዘበ

By ዮሐንስ ደርበው

April 12, 2023

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 4፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ስልታቸውን እየቀያየሩ በበዓል ሰሞን ከሚፈጸሙ የግብይት መጭበርበሮች ሕብረተሰቡ እንዲጠነቀቅ የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት አሳሰበ፡፡

የአገልግሎቱ የኮሙኒኬሽን እና ሕዝብ ግንኙነት ሥራ አስፈጻሚ እንዳለ አሰፋ እንዳሉት÷ በርካቶች እንደአቅማቸው በዓላትን ለማሳለፍ ግብይት ሲፈጽሙ ያለአግባብ ሃብት ለማግኘት የሚጥሩም አሉ፡፡

አጭበርባሪዎች የተለያየ ስልት ስለሚጠቀሙ ሕብረተሰቡ በየትኛውም እንቅስቃሴ እና ግብይት እንዲጠነቀቅም ጠይቀዋል፡፡

ሕብረተሰቡ ሙሉ ትኩረቱን ለበዓል አስፈላጊ አቅርቦትን ለመሸመት ሲጣደፍ በሐሰተኛ ገንዘብ የሚገበያዩ እንዳያጋጥሙት መጠንቀቅ አለበት ብለዋል፡፡

በሌላ በኩል በበዓል ሰሞን የማኅበራዊ ሚዲያዎችን በመጠቀም ማጭበርበሮች እንደሚፈጸሙም ጠቁመዋል፡፡

የተለያዩ ተቋማትን ሎጎ፣ ተመሳሳይ መልዕክቶችን እና ምልክቶች በሕገወጥ ሁኔታ በመጠቀም “እንኳን አደረሳችሁ፣ ለበዓል ስጦታዎች ተመቻችተዋል፣ ይህን ለማድረግ ከታች በተመለከተው ሊንክ ይግቡ፣ እኛ የምንልዎትን እየተከተሉ ያድርጉ” በማለት የተለያዩ ተለዋዋጭ ስልቶችን በመጠቀም የማጭበርበር ድርጊቶች እንደሚፈጸሙ አመላክተዋል።

በመሆኑም ክስረት ከመድረሱ በፊት በዓሉን በሰላማዊ ሁኔታ ለማሳለፍ በእያንዳንዱ ግብይት እና እንቅስቃሴ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

ሕብረተሰቡ አጠራጣሪ ሁኔታዎችን ሲመለከት ለጸጥታ አካላት ጥቆማ እንዲሰጥ እና በቀላሉ ወንጀሉን ለመከላከል እንዲተባበር ጠይቀዋል፡፡

በዮሐንስ ደርበው

#Ethiopia

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!