የሀገር ውስጥ ዜና

በባቡር መሠረተ ልማት ዝርፊያ የተጠረጠሩ ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር ዋሉ

By Alemayehu Geremew

May 15, 2023

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮ-ጅቡቲ ባቡር ትራንስፖርት መሠረተ ልማት ላይ ዝርፊያ በመፈፀም የተጠረጠሩ ሰባት ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የገላን ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያ አስታውቋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ ከኅብረተሰቡ በደረሰ ጥቆማ መሠረት በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የኢትዮ-ጅቡቲ ባቡር ትራንስፖርት መረጃ ያመላክታል፡፡

ግለሰቦቹ “ኬ37” ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የባቡር ሃዲዱን አቅፎ የሚይዘውን ብሎን በኅገ-ወጥ መንገድ በመፍታት እንዲሁም ሌሎች መሠረተ ልማቶች ላይ ስርቆት በመፈፀም ተጠርጥረው ነው በቁጥጥር ስር የዋሉት፡፡

የገቢና ወጪ የጭነት አገልግሎት በከፍተኛ ሁኔታ ከሚሰጥበት እንዶዴ ጣቢያ ጀምሮ ባሉ የባቡር መስመሩ አካላት ማለትም ኬ36፣ ኬ37፣ ኬ38፣ ኬ39 እና ኬ40 አካባቢዎች ላይ ተደጋጋሚ ስርቆት የሚፈፀምባቸው መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

ችግሩን ከመሰረቱ ለመቅረፍም የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የባቡር ዲቪዥን መምሪያ፣ የገላን ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያ፣ የኢዲአር ሲኒየር ሴኩሪቲ ዳይሬክተርና ማናጀር ከሕብረተሰቡ ጋር መምከራቸው ተገልጿል፡፡

የአካባቢው ነዋሪዎች የሚከናወኑ ስራዎችን በቅርበት እንደሚደግፉ አረጋግጠዋል፡፡