240 ሺህ ለሚደርሱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመራቂዎች የመውጫ ፈተና ሊሠጥ ነው
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 15፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) 240 ሺህ ለሚደርሱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች በበይነ-መረብ የመውጫ ፈተና ለመሥጠት መዘጋጀቱን የትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
የትምህርት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እንደገለጹት ÷ በ2015 ዓ.ም በመጀመሪያ ዲግሪ ፕሮግራም ለሚመረቁ ተማሪዎች የመውጫ ፈተና ለመሥጠት ብሉ -ፕሪንት ተዘጋጅቷል፡፡
የመውጫ ፈተና የክፍያ ተመን ረቂቅ መመሪያ መዘጋጀቱንም ዛሬ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት ሪፖርት አብራርተዋል፡፡
የመውጫ ፈተና ስትራቴጂ ማስፈፀሚያ መመሪያ እና የድርጊት መርሐ-ግብር ዝግጅት መጠናቀቁንም ነው የገለጹት፡፡
በመውጫ ፈተና የሚካተቱ የትምህርት ዓይነቶች ተለይተው በቅድመ-ምረቃ በሚሰጡ በሁሉም የትምህርት መስኮች የፈተና ንድፍ ማሳያ መዘጋጀቱን ማስረዳታቸውንም የምክር ቤቱ መረጃ ያመለክታል፡፡