ኢትዮጵያ በሚገኙ 5 ዓለም አቀፍ ት/ ቤቶች ነጻ የትምህርት እድል ሊሰጥ ነው
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 18፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮጵያ የሚገኙ አምስት ዓለም አቀፍ የማህበረሰብ ትምህርት ቤቶች የመክፈል አቅም የሌላቸው ተማረዎችን ነጻ የትምህርት እድል ተጠቃሚ ሊያደርጉ መሆኑ ተገለጸ፡፡
ትምህርት ቤቶቹም ሊሴ ገ/ማርያም ፣ ጣሊያን ት/ቤት ፣ ቤንግሃም አካዳሚ ፣ ሳንፎርድ ዓለም አቀፍ ት/ቤትና አሜሪካን ማህበረሰብ ትምህርት ቤቶች መሆናቸው ተገልጿል፡፡
የትምህርት ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር) ከማህበረሰብ ትምህርት ቤቶች ሃላፊዎች ጋር ተወያይተዋል።
በውይይታቸውም÷ የመማር አቀም እያላቸው ከፍለው መማር ያልቻሉ ተማሪዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ በኢትዮጵያ ያሉ የማህበረሰብ ት/ቤቶች 10 በመቶ ተማሪዎችን ተቀብለው እንዲያስተምሩ መስማማታቸው ተገልጿል፡፡
ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር) ይህን ነጻ የትምህርት እድል ለመስጠት ለተስማሙ ትምህርት ቤቶችም ምስጋና አቅርበዋል፡፡
የዓለም አቀፍ ትምህርት ቤቶቹ ርዕሳነ መመህራንና ሃላፊዎች በበኩላቸው÷ የየአገራቸው የትምህርት ፖሊሲ ለሁሉም እኩል የትምህርት እድል እንደሚፈቅድ አንስተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ተማሪዎችንም ተጠቃሚ ለማድረግ ከሚኒስቴሩ ጋር በቅንጅት እንደሚሰሩ ቃል መግባታቸውን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡