ዓለምአቀፋዊ ዜና

የፀጥታው ምክር ቤት በሱዳን አሥቸኳይ የተኩስ አቁም እንዲደረግ ጠየቀ

By Alemayehu Geremew

June 03, 2023

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 26፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በሱዳን አሥቸኳይ የተኩስ አቁም እንዲደረግና ሰብዓዊ አገልግሎቶች እንዲሳለጡ የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ጠየቀ፡፡

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ኒውዮርክ በሚገኘው ዋና መሥሪያ ቤቱ በጉዳዩ ላይ መክሯል፡፡

በዚህም ምክር ቤቱ ሁለቱ የሱዳን ተፋላሚ ኃይሎች በአስቸኳይ ዘላቂ የተኩስ አቁም ሥምምነት ላይ ለመድረስ ምኅዳሩን እንዲያመቻቹ አሳስቧል፡፡

በሱዳን ዘላቂ ፣ አሳታፊ እና ዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ መፍትሄ ላይ ለመድረስ የተቋረጠው ውይይት መቀጠል አለበት ማለቱንም ሲጂቲ ኤን ዘግቧል።

ተሰብሳቢዎቹ በመግለጫቸው ÷ በሱዳን ሕዝብ ፣ በተመድ እና በተባባሪ ሰራተኞች እንዲሁም ሰብዓዊነት ላይ በተሰማሩ አካላት ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን ኮንነዋል፡፡

በተጨማሪም በሕክምና ሠራተኞች ፣ በተቋማት እና በንብረትላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችንና የሰብዓዊ አቅርቦቶችን ዘረፋም በፅኑ ማውገዛቸው ተመልክቷል፡፡

አስቸኳይ የተኩስ አቁም ስምምነቱ በዓለም አቀፉ ኅግ ድንጋጌ እና በተመድ የሰብዓዊ ዕርዳታ መርሆዎች መሠረት ሰብዓዊነትን እና ገለልተኛነትን ማዕከል አድርጎ መፈጸም እንዳለበትም መግለጫው ጠቁሟል፡፡

የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት በጉዳዩ ላይ የአፍሪካ ኅብረትን አመራር በድጋሚ ያደነቀ ሲሆን ፥ የኅብረቱ ፍኖተ ካርታ በሱዳን ያለውን ግጭት ለመፍታት እንደሚያስችልም አረጋግጧል፡፡