Fana: At a Speed of Life!

የሱዳን ተፋላሚ ኃይሎች የ24 ሠዓት የተኩስ አቁም ሥምምነት ደረሱ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 2፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የሱዳን ጦር እና የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ሃይል የ24 ሠዓት የተኩስ አቁም ሥምምነት ላይ መድረሳቸው ተገለጸ፡፡

ከነገ ጀምሮ የሚተገበረውን የተኩስ አቁም ሥምምነት በማስተባበር ረገድ ሳዑዲ አረቢያ እና አሜሪካ ሚናቸውን መወጣታቸው ተጠቁሟል፡፡

ሁለቱ ተፋላሚ ኃይሎች የተኩስ አቁም ሥምምነቱን ከፈረሙበት ሠዓት ጀምሮ ከማንኛውም ዓይነት የተከለከሉ እንቅስቃሴዎች እና የመሣሪያ ጥቃቶች እንደሚታቀቡ ተገልጿል፡፡

ከዚህ ባለፈም በጦር አውሮፕላን ወይም በድሮን ከሚፈጸሙ ድብደባዎች እና ከመሳሰሉት እንዲቆጠቡም የሳዑዲ አረቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡

ማንኛውም ወገን የተኩስ አቁም ሥምምነቱን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ገዢ ቦታ ለመያዝ እና የጦር መሣሪያ በማጓጓዝ የኃይል የበላይነቱን ለማረጋገጥ ከሚደረግ ሩጫ መታቀብ እንዳለበትም ተጠቁሟል፡፡

በሀገሪቷ ሁሉም አካባቢዎች የሰብዓዊ ድጋፍ አቅርቦት እንዳይስተጓጎልም ሁለቱ ኃይሎች የበኩላቸውን ይወጣሉ ተብሏል፡፡

ከነገ ጀምሮ ተግባራዊ የሚሆነው የ24 ሠዓት የተኩስ አቁም ሥምምነት ÷ በጦርነት ምክንያት ተቋርጦ የቆየውን ሰብዓዊ ድጋፍ በድጋሚ ለመጀመር ያስችላል ተብሏል፡፡

በተለይ ጅዳ ላይ ተጀምሮ የነበረውን የተፋላሚ ኃይሎቹን ንግግር እንደገና ለመጀመር እና ዘላቂ የተኩስ አቁም ሥምምነት ላይ ለመድረስ መደላድል እንደሚፈጥር ተሥፋ ተጥሎበታል፡፡

#Ethiopia

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.