20 ሺህ 411 ነጥብ 5 ሜትሪክ ቶን የአፈር ማዳበሪያ ወደ ሀገር ውስጥ ተጓጓዘ
አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 17፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በትናንትናው ዕለት 20 ሺህ 411 ነጥብ 5 ሜትሪክ ቶን የአፈር ማዳበሪያ ወደ ሀገር ውስጥ መጓጓዙ ተገለጸ፡፡
ማዳበሪያው በ439 ተሽከርካሪዎች እና በባቡር ወደ ሀገር ውስጥ መጓጓዙም ተመላክቷል፡፡
የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ÷ በቀጣይ ቀናት ጅቡቲ ወደብ የደረሰውን የአፈር ማዳበሪያ በአጭር ጊዜ ወደ ሀገር ውስጥ አጠቃሎ ለማጓጓዝ እየሠራ መሆኑን ከድርጅቱ ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
የድርጅቱ ዋና ሥራ አሥፈፃሚ በሪሶ አመሎ (ዶ/ር ) ÷ በጅቡቲ የኢትዮጵያ ኤምባሲ፣ የኢትዮ-ጅቡቲ የምድር ባቡር አ.ማ ፣ በኢባትሎ ጅቡቲ ኤም ቲ ኤስ አመራሮችና ሰራተኞች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት ሂደቱን በማሳለጥ ረገድ በትጋት እየሠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ እና የኢትዮ ጅቡቲ የምድር ባቡር አ.ማ በሀገሪቱ ወሳኝ የሚባሉ ግብዓቶችን በፍጥነትና በብዛት ወደ ሀገር ውስጥ ለማጓጓዝ በሚያስችሉ ምቹ ሁኔታዎች ላይ የጋራ ውይይት አድርገዋልም ነው የተባለው፡፡