በበጀት ዓመቱ ከሳይበር ጥቃት 23 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ማዳን መቻሉ ተገለጸ
አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 17፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በ2015 በጀት ዓመት የሳይበር ጥቃቶችን በመከላከል 23 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ማዳን መቻሉን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር አስታወቀ።
የአስተዳደሩ ዋና ዳይሬክተር ሰለሞን ሶካ የ2015 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀምን አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
በመግለጫቸውም በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ 6 ሺህ 959 የሳይበር ጥቃቶች መፈፀማቸውን ጠቁመው÷ ከእነዚህ ውስጥ 6 ሺህ 768ቱ የጥቃት ሙከራዎች መሆናቸውን አንስተዋል፡፡
191 ያህሉ የተሳኩ የሳይበር ጥቃቶች እንደሆኑ የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ÷ ምላሽ የሚፈልጉትን በመለየት ከአጠቃላይ 96 ነጥብ 02 በመቶ ለሚሆኑት ምላሽ መሰጠቱን ገልፀዋል።
በበጀት ዓመቱ በ123 ተቋማት ላይ የዳሰሳ ጥናት መደረጉን ጠቅሰው÷ በዚህም 652 ለሳይበር ጥቃት አጋላጭ ክፍተቶች ተገኝተዋል ብለዋል።
በወንድሙ አዱኛ