Fana: At a Speed of Life!

የኤካ ኮተቤ ሆስፒታል ስነ- አዕምሮ ህክምና ክፍል ለኮቪድ-19 ህሙማን አገልግሎት መስጠት ሊጀምር ነው

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 1፣2012( ኤፍ.ቢ.ሲ) በአዲስ አበባ የኤካ ኮተቤ ሆስፒታል የስነ-አዕምሮ ህክምና ክፍል ለኮሮናቫይረስ (ኮቪድ-19) ህሙማን የህክምና አገልግሎት መስጠት ሊጀምር ነው።

በሆስፒታሉ የስነ-አዕምሮ ህክምና ክፍል ሃላፊ ዶክተር አይዳ ከበደ ÷ሆስፒታሉ  የኮሮናቫይረስ ላለባቸው ሰዎች የህክምና አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል ብለዋል።

ቫይረሱ ተገኝቶባቸው ወደ ሆስፒታሉ የሚመጡ አንዳንድ ታካሚዎች አላስፈላጊ ጭንቀት፣ ፍርሃት፣ መረበሽ እንዲሁም የእንቅልፍ ማጣት እንደሚስተዋልባቸው ገልጸዋል።

በዚህም የህክምና አገልግሎቱ የተለያዩ የስነ-ልቦና እና የስነ-አዕምሮ ችግሮች ለታየባቸው ህሙማንም አገልግሎት እየተሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል ።

በኢትዮጵያ ቫይረሱ  እንደተከሰተ በየክፍሉ የስነ-ልቦና ህክምና እየተሰጠ የነበረ ቢሆንም ለኮቪድ-19  መከላከያ የሚደረገው ልብስ ከስነ-ልቦና ምክክር ጋር ምቹ ባለመሆኑ በአሁኑ ወቅት ህክምናው በስልክ እየተሰጠ  ነው መሆኑን አንስተዋል ።

ይህንንም አገልለግሎት  በማሻሻል ሆስፒታሉ ለስነ-አዕምሮና ስነ-ልቦና ህክምና እያስገነባ ያለው ክፍል ተጠናቆ ስራ  እንደሚጀምር ነው የገለጹት።

የአዕምሮ ህክምና ክፍሉ የተወሰኑ የማጠናቀቂያ ስራዎች አልቀው በቀጣይ ሳምንት አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምርም  ሃላፊዋ ገልጸዋል።

የኮሮና ወረርሽኝ ከበሽታው በተጨማሪ የስነ-ልቦና መረበሽ ችግር እየሆነ መምጣቱንም ዶክተር አይዳ ጠቁመው÷ለችግሩ መባባስ በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች የሚለቀቁ ትክክለኛነታቸው ያልተረጋገጠ መረጃዎችም ምክንያት መሆናቸውንም ተናግረዋል።

በመሆኑም ከአለም የጤና ድርጅት፣ የጤና ሚኒስቴር እንዲሁም ከጤና ባለሙያዎች የሚሰጡ መረጃዎችንና ምክሮችን መከተል ተገቢ እንደሆነ  ገልጸው÷  ሳይንሳዊ ምክሮችን በመከተልና ፍርሃትን በማስወገድ በሽታ የመከላከል አቅምን ማጠናከር እንደሚያስፈልግም መክረዋል።

ታማሚዎች አገግመው ከሆስፒታሉ ከወጡ በኋላ በአካል በመምጣት አገልግሎት ማግኘት እንደሚችሉም ነው የተናገሩት።

ሃላፊዋ  አያይዘውም በጤና ሚኒስቴር የሚገኝ የስነ-ልቦና እና ስነ-አዕምሮ ህክምና አድቫይሰሪ ካውንስል በተለያዩ ለይቶ ማቆያ ለሚገኙ ሰዎች የስነ-ልቦና ድጋፍና እዳታ እያደረገላቸው  ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

ትኩስ መረጃዎችን በፍጥነት ለማግኘት የቴሌግራም ገፃችንን ሰብስክራይብ ያድርጉ!

https://t.me/fanatelevision

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.