ግብርናችን ለማዘመን በምናደርገው ጥረት የውሃና ኢነርጂ ግብዓት ወሳኝ ነው-ግርማ አመንቴ (ዶ/ር)
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 26፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ግብርናን ለማዘመን እና ለማሻገር በምናደርገው ጥረት የውሃና ኢነርጂ ግብዓት ወሳኝ ነው ሲሉ የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡
በግብርና ሚኒስትሩ የተመራው የግብርና ሚኒስቴር አመራሮች ቡድን የውሃና ኢነርጂ አውደ ርዕይን ጎበኝቷል።
በዚህ ወቅት ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ(ዶ/ር)÷ በአውደ ርዕዩ ላይ የታዩ እና እየተፈጠሩ ያሉ የቴክኖሎጅ አቅሞች ለግብርናችን ትልቅ ግብዓት ናቸው ብለዋል።
እስካሁን በተከናወኑ ስራዎች የውሃ መበልጸግ አቅም እንዲጨምር፣የገጸምድር ውሃ ፍሰት እንዲስተካከል ፣የአፈር መጠን ላይ መሻሻል እንዲኖር እና የውሃ ጥራት እንዲጨምር ማድረግ መቻሉን አብራርተዋል፡፡
በአውደ ርዕዩ ዝናብ ላይ ጥገኛ የሆነውን ግብርና በሚቀጥሉት አመታት የተለያዩ የውሃ አማራጮችን በመጠቀም መስኖ ማልማት የሚቻልበት አቅም እየተፈጠረ መሆኑን ማየት ችለናል ብለዋል፡፡
ግብርናችን ለማዘመን እና ለማሻገር በምናደርገው ጥረት የውሃና ኢነርጂ ግብዓት ወሳኝ ከመሆኑ ባሻገር የሀገራችን ብልጽግና ለማረጋገጥም ትልቅ አቅም እንዳለው አመላክተዋል፡፡
በቀጣይም እነዚህን ቴክኖሎጂዎች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ በጋራ እንደሚሰራም ማረጋገጣቸውን ከግብርና ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡