ሙስናን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ ጥሪ ቀረበ
አዲስ አበባ፣ መስከረም 6፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የተቋማትን አሰራር ግልፅና ተጠያቂነት ያለበት በማድረግ ሙስናን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ሁሉም የድርሻውን መወጣት እንዳለበት የፌዴራል የሥነ- ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ።
የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ሳሙኤል ኡርቃቶ (ዶ/ር) በአንዳንድ ተቋማት ሙስናን ለመከለካል የሚያስችሉ ተስፋ ሰጪ ጅምሮች መኖራቸውን ጠቁመው የጸረ ሙስና ትግሉ በሁሉም ዘንድ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል፡፡
በየደረጃው ያሉ የተቋማት አመራሮች ራሳቸውን ከሙስና ነፃ በማድረግ የተቋሙ አሰራርም ሙስና የሌለበት መሆኑን ማረጋገጥና መከታተል ይጠበቅባቸዋል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትና ሌሎችም አስፈፃሚውን የሚቆጣጠሩ አካላት የኦዲት ግኝቶችን በማጤንና ለሙስና የተጋለጡ አለመሆናቸውን ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል ነው ያሉት።
የሙስና ድርጊትን በተመለከተ የዜጎች የጥቆማ አሰጣጥ ደኅንነቱ በተጠበቀ መልኩ በዲጂታል የመረጃ ማዕከል እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው÷ በቀጣይነትም መረጃና ጥቆማ መስጠታቸውን እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል።