ኢትዮጵያ በ “ኤክስፖ 2023 ዶሃ ዐውደ- ርዕይ” እየተሳተፈች ነው
አዲስ አበባ፣ መስከረም 22፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ በመካከለኛው ምሥራቅ ‘አረንጓዴ በረሃ፣ የተሻለ አካባቢ’ በሚል መሪ ሐሳብ በዶሃ ቢዳ ፓርክ በተከፈተው ዓለም አቀፍ የሆርቲካልቸር ዐውደ- ርዕይ ላይ እየተሳተፈች ነው፡፡
በኳታር አሚር ሼክ ታሚም ቢን ሃማድ አል ታኒ የተከፈተው ዐውደ- ርዕዩ በረሃማነትን የመዋጋት ዓላማ ያለው ሲሆን÷ ዘመናዊ ግብርናን፣ ቴክኖሎጂ እና ፈጠራን፣ የአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ እና ዘላቂነትን ለመደገፍ ያለመ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በተጨማሪም የሆርቲካልቸር ዘርፍን ለማስተዋወቅና ለማሳደግ ያለመ ዐውደ- ርዕይ መሆኑን በኳታር የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመላክታል፡፡
ዐውደ- ርዕዩ በሁለት ዓመት አንድ ጊዜ እንደሚካሄድም ነው የተገለጸው፡፡
ለ179 ቀናት በሚቆየው ዐውደ- ርዕይ ላይ የግል ኩባንያዎችን ጨምሮ 80 የሚጠጉ ሀገራት፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና ዓለም አቀፍ የዘርፉ ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው፡፡
የእርሻ ልማትና ሆርቲካልቸር ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር) ፣ በኳታር የኢትዮጵያ አምባሳደር ፈይሰል አልይ እና ሌሎች የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በዐውደ- ርዕዩ የመክፈቻ ሥነ- ሥርዓት ላይ ተሳትፈዋል፡፡