የገጠር መንገድ ተደራሽነትን በማስፋት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ፕሮጀክት ይፋ ሆነ
አዲስ አበባ፣ ሕዳር 17፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በ60 ቢሊየን ብር የገጠር መንገድ ተደራሽነትን በማስፋት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ፕሮጀክት ይፋ መሆኑን የከተማና መሠረተ-ልማት ሚኒስቴር አስታወቀ።
የፕሮጀክቱን አተገባበርና ዓላማ በማስመልከት ከባለድርሻ አካላት ጋር ዛሬ በአዲስ አበባ በተካሄደው መድረክ እንደተገለጸው÷ ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ የሚውለው 60 ቢሊየን ብር በመንግሥትና በዓለም ባንክ እገዛ ይሸፈናል፡፡
የከተማና መሠረተ-ልማት ሚኒስትር ዴዔታ ወንድሙ ሴታ (ኢ/ር) በመድረኩ ላይ እንዳሉት÷ ለአራት ዓመታት የሚተገበረው ፕሮጀክት የመንገድ ተደራሽነትን ከማስፋት ባለፈ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጥሩ አማራጭ ነው፡፡
በተለይም ለግብርና ልማትና ምርታማነት፣ ለማዕድን ልማት እንዲሁም የግብርና ግብዓቶችን በቀላሉ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ የላቀ አበርክቶ ይኖረዋል ብለዋል፡፡
ፕሮጀክቱ የመንገድ ተደራሽነት በሌለባቸው አካባቢዎች እንደሚከናወንና በዕቅዱ መሠረትም 1 ሺህ 200 ድልድዮች ይገነባሉ ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
በፕሮጀክቱ ምርታማነትንና የገበያ ተደራሽነትን የማስፋት ሥራም ልዩ ትኩረት ተሰጥቶታል ነው ያሉት፡፡