ስፓርት

የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀንን በማስመልከት በጂግጂጋ የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር ተካሄደ

By ዮሐንስ ደርበው

December 05, 2023

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 25፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) 18ኛውን የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በዓልን በማስመልከት በጂግጂጋ ከተማ የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር ተካሂዷል፡፡

በወንዶች በተደረገው የሩጫ ውድድር ከጅግጅጋ አትሌቲክስ ፕሮጀክት የተወከለው አትሌት አሕመድ መሐመድ 1ኛ፣ ከጅግጅጋ አትሌቲክስ ፕሮጀክት የተወከሉት አትሌት በረከት መሐመድ 2ኛ እንዲሁም አትሌት መሐመድ አሕመድ 3ኛ በመውጣት ውድድሩን አጠናቀዋል፡፡

እንዲሁም በሴቶች በተደረገው የሩጫ ውድድር ከጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ የተወከለችው አትሌት ቃልኪዳን አይችሌ ቀዳሚ በመሆን ውድድሩን አሸንፋለች፡፡

በርቀቱ ከጅግጅጋ አትሌቲክስ ፕሮጀክት የተወከለችው ዝናሽ ትዕግሥቱ 2ኛ፣ ከጅማ ዩኒቨርሲቲ የተወከለችው አትሌት በሻቱ ተካ 3ኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቅቀዋል፡፡

18ኛው የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በዓል ከሕዳር 25 እስከ ሕዳር 29 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ በፌዴሬሽን ምክር ቤት አስተባባሪነትና በሶማሌ ክልል አስተናጋጅነት “ብዝኅነትና እኩልነት ለሀገራዊ አንድነት” በሚል መሪ ሐሳብ በጂግጂጋ ከተማ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ይከበራል።

በዚህም ሕዳር-25 የወንድማማችነት፣ ሕዳር-26 የብዝኃነት፣ ሕዳር-27 የአብሮነት፣ ሕዳር-28 የመደመር፣ ሕዳር-29 የኢትዮጵያ ቀን በሚሉ መሪ ስያሜዎች በተለያዩ ዝግጅቶች መከበር ጀምሯል።

#Ethiopia

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!