የሀገር ውስጥ ዜና

በአውስትራሊያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ለ2ኛ ትውልድ ኢትዮጵያውያን የመመዝገቢያ ሊንክ አስተዋወቀ

By Alemayehu Geremew

January 09, 2024

አዲስ አበባ፣ ታኅሣስ 30፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በአውስትራሊያ ካምቤራ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በአውስትራሊያ፣ ኒውዚላንድና በቀጣናው ሀገራት ለሚኖሩ 2ኛ ትውልድ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው ለመመለስ የሚመዘገቡበት አማራጭ የበይነ መረብ ማስፈንጠሪያ አስተዋወቀ፡፡

ኤምባሲው ከላይ በተገለጹት ሀገራት እና በቀጣናው የሚኖሩ የሁለተኛው ትውልድ ኢትዮጵያውያን https://docs.google.com/…/1FAIpQLSc…/viewform በሚለው የበይነ መረብ አማራጭ በመጠቀም እንዲመዘገቡ አስታውቋል፡፡

ለበለጠ መረጃም +61405332934 በሚለው ሥልክ ቁጥር ወይም canberra.consular@mfa.gov.et በሚል የቀረበውን የኢሜይል አማራጭ በመዳሰስ ተጨማሪ መረጃዎችን ማግኘት እንደሚቻልም ጠቁሟል፡፡

ኤምባሲው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሁለተኛው ትውልድ የኢትዮጵያ ዲያስፖራዎች በሦስት ዙር ወደ ሀገራቸው በመግባት ኢትዮጵያን እንዲጎበኙ እና የባሕል መሠረታቸውን እንዲያውቁ ጥሪ ማቅረባቸውንም አስታውሷል፡፡

የመጀመሪያው ዙር የጉዞ መርሐ ግብር መጀመሩንና በመላው ዓለም የሚገኙ በርካታ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያንም ወደ ሀገራቸው እየገቡ እንደሚገኝም ጠቅሷል።

የዚህ ታላቅ ሀገራዊ ጥሪ አካል በመሆን የሀገራችሁን ወግ፣ ዕሴት፣ ባሕል፣ የዘመናት አኩሪ ታሪክ፣ አስደናቂ የመልክዓ ምድር ገጽታና ውብ ተፈጥሮን በማወቅ ለመላው ዓለም ሕዝቦች ሀገራችሁን አስተዋውቁ ሲልም ነው ጥሪውን ያቀረበው፡፡