የሀገር ውስጥ ዜና

በውኃ አካላት ላይ የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው

By Alemayehu Geremew

January 10, 2024

አዲስ አበባ፣ ጥር 1፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ወደብን ጨምሮ በውኃ አካላት ላይ የማሪን ቴክኖሎጂን በመጠቀም የአየር ትንበያ አገልግሎት መስጠት የሚያስችለውን ዝግጅት እያደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ።

የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ እንዳሉት÷ የአየር ትንበያ አገልግሎት ለአቪዬሽን ዘርፉ የጀርባ አጥንት ሆኖ እያገለገለ መሆኑን አንስተዋል፡፡

እንዲሁም ወደብን ጨምሮ በውኃ አካላት ላይ የውኃ ትራንስፖርትን ማሳለጥ የሚችል የማሪን ቴክኖሎጂን በመጠቀም የአየር ትንበያ አገልግሎት መስጠት የሚያስችለውን ዝግጅት እያደረገ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

ኢትዮጵያ ለበርካታ ዓመታት የባሕር በር የሌላት ሆና በመቆየቷ ቴክኖሎጂውን ወደ ሥራ ማስገባት አለመቻሏን ለኢዜአ የተናገሩት ዋና ዳይሬክተሩ÷ ከሶማሊ ላንድ ጋር የባሕር በር ለማግኘት የተደረገው ስምምነት ቴክኖሎጂውን ለመጠቀም ምቹ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል።

ኢትዮጵያ የዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት አባልና የአፍሪካ ሊቀ-መንበር እንደመሆኗ ÷ ዓለምአቀፍ የአየር ትንበያ ልውውጦችን በማድረግ ተዓማኒነት ያለው መረጃ መስጠት የሚያስችላት አቅም እንዳለት ጠቁመዋል፡፡

በውኃ አካላት ላይ የሚተከሉ የሚቲዎሮሎጂ መረጃ መሰብሰቢያ ጣቢያዎችን በመትከል አገልግሎት ለመስጠት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ነው ያረጋገጡት፡፡