Fana: At a Speed of Life!

የካናዳ መንግስት በኢትዮጵያ የአካል ጉዳተኞች አካቶ ትምህርት ፕሮጀክትን ውጤታማ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ገለፀ

አዲስ አበባ፣ ጥር 30፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የካናዳ መንግስት በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የአካል ጉዳተኞች አካቶ ትምህርት ፕሮጀክትን ውጤታማ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን በኢትዮጵያ የካናዳ አምባሳደር ጆሺኣ ታባህ(ዶ/ር) ገለፁ፡፡

አምባሳደሩ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ በትብብር ስምምነት የሚከናወኑ ተግባራትን ጎብኝተዋል።

አምባሳደሩ እንደገለጹት ፥ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽንና ከካናዳው ኪዩንስ ዩኒቨርሲቲ ጋር ለ10 ዓመታት የሚተገበር የ25 ሚሊየን ዶላር ፕሮጀክት ተግባራዊ እያደረገ ነው።

የፕሮጀክቱ አፈፃፀምን በተመለከተ ከጎንደር ዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ አመራሮች ጋር አምባሳደሩ የተወያዩ ሲሆን ÷ የሁለቱ ሀገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የካናዳ መንግስት ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት ቢንያም ጫቅሉ(ዶ/ር) ÷ ዩኒቨርሲቲው ከካናዳ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በትብብር እየሰራ መሆኑን አንስተዋል፡፡

ይህም በትምህርት ዘርፉ የሚሰራው ስራ የሚደነቅ መሆኑንም ነው የገለጹት።

በአካል ጉዳተኞች አካቶ ትምህርት የ10 ዓመት ፕሮጀክት ተግባራዊ መሆኑን የገለፁት ምክትል ፕሬዚዳንቱ ፥ በትምህርት ዘርፍ ሁለቱ ተቋማት የልምድ ልውውጥ ያደርጋሉም ብለዋል።

የካናዳ ዩኒቨርሲቲዎች ከጎንደር ዩኒቨርሲቲ ጋር የጀመሯቸው የትብብር ስራዎች ውጤታማ እንዲሆኑ የተጠናከረ ጥረት እንደሚደረግም ጠቁመዋል፡፡

በሹመት አለማየሁ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.