የሀገር ውስጥ ዜና

ሀሰተኛ ሠነዶችን ሲያዘጋጁ የነበሩ 4 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ

By Melaku Gedif

March 11, 2024

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 2፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በመኖሪያ ቤት ውስጥ ሀሰተኛ ሠነዶችን ሲያዘጋጁ የነበሩ አራት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ፡፡

ተጠርጣሪዎቹ የተያዙት በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ ልዩ ቦታው ቦሌ ሚካኤል ተብሎ በሚጠራው አካባቢ መሆኑ ተገልጿል፡፡

ግለሰቦቹ የተለያዩ ሀሰተኛ የመንግስትና የግል ተቋማት ሠነዶችን እንደሚያዘጋጁ ህብረተሰቡ ለፖሊስ በሰጠው ጥቆማ መሰረት በህግ አግባብ በተደረገ ብርበራ ነው በቁጥጥር ስር የዋሉት፡፡

ልዩ ልዩ ሃሰተኛ ሠነዶች፣ ሰነዶቹን ለማዘጋጀት የሚጠቀሙባቸው ሃሰተኛ ማህተም እና ቲተሮች እንዲሁም ሁለት ላፕቶፕ ኮምፒውተሮች መያዛቸውንም የፖሊስ መረጃ ያመላክታል፡፡

ሰነዶቹን በማዘጋጀት ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር በዋሉት አራት ግለሰቦች ላይ ምርመራ የማጣራት ሥራ መቀጠሉም ተጠቁሟል፡፡