የሀገር ውስጥ ዜና

የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ጋር ለመስራት ተስማማ

By Shambel Mihret

March 12, 2024

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 3፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ፣ ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣንና ከኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ጋር በትብብር ለመስራት ስምምነት ተፈራርሟል፡፡

ስምምነቱን የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ርዕሰ አካዳሚ ዛዲግ አብርሃ፣የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ተጠባባቂ ዳይሬክተር አቶ ፋሲካው ሞላ እና የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ምክትል ዳይሬክተር ወ/ሮ ሃና ወልደገብርኤል ፈርመውታል፡፡

አቶ ዛዲግ አብርሃ÷ስምምነቱ በተቋማቱ መካከል ያለውን ትብብር የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በኢትዮጵያ ጠንካራ እና ብቁ የሆነ አመራርን ማፍራት ሲቻል የሀገሪቱን ብልጽግና ማረጋገጥ እንደሚቻልም አንስተዋል፡፡

በኢትዮጵያ ዘላቂ ልማት እንዲረጋገጥና የሀገርና የህዝብ ችግርን ለመፍታት ተቋማት ተቀናጅተው መስራት እንደሚጠበቅባቸውም መገለጹን የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ መረጃ ያመላክታል፡፡

ስምምነቱ ተጨባጭ እድገትን ለማምጣት የሚደረገውን እንቅስቃሴ እውን ለማድረግ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረውም ተገልጿል፡፡