በኢትዮጵያ የአስቸኳይ ሰብዓዊ እርዳታ የሚውል የ80 ሚሊየን ዶላር ድጋፍ ይፋ ሆነ
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 7፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮጵያ የአስቸኳይ ሰብዓዊ እርዳታ የሚውል የ80 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር ድጋፍ ይፋ ማድረጉን የአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት (ዩኤስኤይድ) ገለፀ።
ዛሬ በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኤምባሲ በሰጠው መግለጫ÷በኢትዮጵያ አስቸኳይ የሰብዓዊ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው የሚውል ተጨማሪ የ80 ሚሊየን ዶላር መመደቡን ጠቅሷል።
የሰብዓዊ ጉዳዮች ቢሮ የዋና ዳይሬክተሯ ረዳት ሶናሊ ኮርዴ÷ በትግራይ እና አፋር ክልሎች ባደረጉት ጉብኝት አስቸኳይ እርዳታ ለሚፈልጉ ሰዎች ተደራሽ ለማድረግ ከተራድኦ ድርጅቶች በኩል ጥረቶች እንዳሉ መገንዘባቸውን ተናግረዋል።
ሰብዓዊ እርዳታው በቂ እንዳልሆነና በሁሉም አካባቢ እርዳታውን ተደራሽ ማድረግ ላይ ተግዳሮቶች መኖራቸውንም አንስተዋል፡፡
በትግራይ እና አፋር ክልሎች በርካታ ድጋፍ የሚሹ ሰዎች መኖራቸውን ስለማረጋገጣቸው ነው የገለጹት።
በዚህም የተራድኦ ድርጅቶች ሰብዓዊ ድጋፋቸውን እንዲያሳድጉ ጥሪ አቅርበው÷ ሰብዓዊ እርዳታ ለሚሹ ወገኖች ተደራሽ እንዲሆን ዩኤስኤይድ ተጨማሪ የ80 ሚሊየን ዶላር ድጋፍ ስለመወሰኑ አመላክተዋል።
ገንዘቡ የምግብ እጥረት ለገጠማቸው ከ1 ነጥብ 5 ሚሊየን በላይ ለሚሆኑ ከአምስት ዓመት በታች ለሆኑ ህፃናት እና 600 ሺህ ለሚሆኑ ነብሰ ጡር እናቶች አስቸኳይ የሰብዓዊ ድጋፍ ይውላል ብለዋል።
በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ በበኩላቸው÷ አሜሪካ የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ እንደምትቀጥል ተናግረዋል።
ከታህሳስ 2023 ጀምሮ በትግራይ፣ አማራ፣ አፋር፣ ኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች ለ2 ነጥብ 4 ሚሊየን ሰዎች አስቸኳይ የምግብ እርዳታ መደረጉን አስታውሰዋል፡፡
ከዚህ በፊት የህዝቡን ህይወት ለማሻሻል ሲሰሩ የነበሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልፀዋል።
በታሪኩ ለገሰ