Fana: At a Speed of Life!

የምስራቅ አፍሪካ የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች ማህበር ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ተጠናቀቀ

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 25፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ላለፉት አራት ቀናት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የነበረው የምስራቅ አፍሪካ ሀገሮች የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች ማህበር ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ተጠናቋል፡፡

በጉባኤው ኢትዮጵያ የሁለት ዓመት ሪፖርቷን ያቀረበች ሲሆን የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በሥነምግባር ግንባታ፣ በሙስና መከላከልና የተመዘበረ ሀብት ማስመለስ ላይ የተከናወኑ ሥራዎችና የተገኙ ውጤቶች ቀርበዋል፡፡

በተጨማሪም ኬንያ፣ ታንዛኒያ፣ ሩዋንዳ፣ ጅቡቲ፣ ኡጋንዳ እና ቡሩንዲ ሪፖርታቸውን አቅርበው በመድረኩ ውይይት ተካሂዶበታል።

በመድረኩ የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ከሀገር የሸሹ እና የተመዘበሩ ሀብቶችን ለማስመለስ እንዲሁም ሀገራቱ መረጃ መለዋወጥ በሚችሉባቸው ጉዳዮች ላይ ተወያይተው የጋራ አቋም መያዛቸው ተገልጿል።

በተጨማሪም በመድረኩ የተባበሩት መንግስታት እና የአፍሪካ ህብረት የፀረ-ሙስና ስምምነቶችን ተግባራዊ በሚያደርግበት ጉዳይ ላይ እንዲሁም በህብረቱ አባል ሀገራት የፀረ-ሙስና ትግል ላይ ያጋጠሙ ተግዳሮቶች ምክክር ተደርጎባቸዋል፡፡

ሩዋንዳ ለቀጣይ ሁለት አመታት የምስራቅ አፍሪካ ሀገሮች የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች ማህበር ሊቀመንበርነትን ለኡጋንዳ ያስረከበች ሲሆን ኬንያ በምክትል ፕሬዚዳንትነት መሰየሟ ተጠቅሷል፡፡

የቀጣዩ የአባል ሀገራት የምክክር መድረክ በኡጋንዳ እንደሚካሄድ መገለፁን ከፌደሬራል ስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.