የሀገር ውስጥ ዜና

ሕዝቡ በሰላም፣ በአንድነትና በልማት ላይ በማተኮር እጅ ለእጅ ተያይዞ መስራት አለበት – ጠ/ሚ ዐቢይ (ዶ/ር)

By Melaku Gedif

May 08, 2024

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 30፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ሕዝቡ በሰላም፣ በአንድነትና በልማት ላይ በማተኮር እጅ ለእጅ ተያይዞ መስራት አለበት ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።

በነቀምቴ ከተማ ወለጋ ስታዲየም የለውጡን መንግስት የሚደግፍ ሰልፍ ”ወለጋ የሰላምና የብልጽግና ምድር” በሚል መሪ ሃሳብ የአራቱ ወለጋ ዞኖች ነዋሪዎች የተሳተፉበት ሰልፍ ተካሂዷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) በወቅቱ ባስተላለፉት መልዕክት÷ ህዝቡ በሰላም፣ በአንድነትና በልማት ላይ እንዲያተኩር ጥሪ አቅርበዋል።

ሰላም የሁሉ ነገር መሰረት መሆኑን ጠቅሰው÷ ”ሰው ውስጡ ሰላም የሆነ፣ ሀገሩ ሰላም ከሆነ ልክ እንደ ዛሬ በፍቅርና በወንድማማችነት መንፈስ ተገናኝቶ መለያየት ይችላል” ነው ያሉት።

ከሁሉም በላይ ለልማት፣ የተለያየ ሀሳብ ለማመንጨት አንድነት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመው÷ “ትውልዱን የሚጎዳ ነገር ከማድረግ በመቆጠብ በመመካከር አንድነትን ማጽናት ይገባል” ብለዋል።

ከኢኮኖሚ አኳያ ከለውጡ በፊት ብዙ ችግር ተደቅኖ እንደነበር አስታውሰው÷ ከለውጡ በኋላ ግን በብዙ ችግሮች ውስጥ ትልቅ የኦኮኖሚያዊ ለውጥ እየተመዘገበ መሆኑን አብራርተዋል።

በለውጡ ዓመታት በተሰራ ሥራ ግብርናንና ከተማን የሚለውጥ፣ ሀገር የሚያሸግር ኢኮኖሚ እየተመዘገበ መሆኑን አስረድተዋል።

”የጀመርነውን ስራ ከግብ ለማድረስ የሚያስቆመን ሃይል አይኖረም፣ በንጹህ ልባችን ሀገር ለመለወጥ ነው እየሰራን ያለነው” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፡፡

‘አሁንም እንደ ትናንቱ በሙሉ ልብ እናገራለሁ፤ የኢትዮጵያን ብልጽግና እናረጋግጣለን፣ አንድነቷም ይጠበቃል፣ በአፍሪካ የምትከበር ሀገር ትሆናለች” ብለዋል።

”ልማትና እድገታችንን የሚያፋጥን ሰላም እንዲጸና መትጋት እንደሚገባ ለሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ መግለጽ እፈልጋለሁ” ሲሉም መናገራቸውን የዘገበው ኢዜአ ነው፡፡

”ወለጋን መቀየር እንፈልጋለን፣ እቅዳችን በጠላት ዓላማ እንዳይደናቀፍም ህዝባችን ከጎናችን መቆም ይገባዋል” ነው ያሉት፡፡