ከ2 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመቱ የሞባይል ቀፎዎችንና ካርዶችን ለግል ጥቅሙ አውሏል የተባለው ሰራተኛ በእስራት ተቀጣ
አዲስ አበባ፣ ታሕሣሥ 15፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ከ2 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመቱ የሞባይል ቀፎዎችንና ካርዶችን ለግል ጥቅም አውሏል የተባለው የቀድሞ የህዳሴ ቴሌኮም አክሲዮን ማህበር ሰራተኛ በእስራት መቀጣቱ ተነግሯል፡፡
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የድሬዳዋ ምድብ ጅግጅጋ ተዘዋዋሪ ወንጀል ችሎት ዛሬ በዋለው ቀጠሮ መስፍን ኣሰፋ በተባለ ተከሳሽ ላይ የግራ ቀኝ ማስረጃዎች መርምሮ ጥፋተኛ በማለት የጽኑ እስራትና የገንዘብ መቀጮ ውሳኔ አስተላልፎበታል።
በፍትህ ሚኒስቴር ድሬዳዋ ቅርጫፍ ጽህፍት ቤት ዐቃቤ ህግ በተከሳሹ ላይ በ1996 ዓ/ም የወጣውን የወንጀል ህግ አንቀጽ 676 ንዑስ ቁጥር 1 ስር የተመለከተውን ድንጋጌ መተላለፉን ጠቅሶ ሚያዚያ 22 ቀን 2015 ዓ.ም ዝርዝር ክስ አቅርቦበት ነበር።
በዚህ በቀረበበት ክስ ዝርዝር ላይ እንደተመላከተው ተከሳሽ ተገቢ ያልሆነ ብልጽግና ለራሱ ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ የህዳሴ ቴሌኮም አክሲዮን ማህበር የምስራቅ ዲስትሪክት በጎዴ አካባቢያዊ ጽህፈት ቤት ሱፐርቫይዘር ሆኖ በሚያገለግልበት ወቅት ከጳጉሜን 3 ቀን 2003 ዓ.ም እስከ ሚያዚያ 14 ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ ከአክሲዮን ማህበሩ የተረከባቸውን የተለያዩ ዋጋ ያላቸው የሞባይል ካርዶችን፣ ሲም ካርዶች እና የሞባይል ቀፎዎች ጠቅላላ ዋጋው 2 ሚሊየን 703 ሺህ 635 ብር የሆነ ንብረት ለአክሲዮን ማህበሩ ገቢ ማድረግ ሲገባው የተጣለበትን እምነት ወደ ጎን በመተው ለግል ጥቅሙ ያዋለ መሆኑ ተጠቅሶ ከባድ የእምነት ማጉደል ወንጀል ክስ ቀርቦበት ነበር።
ተከሳሹ በጅግጅጋ ተዘዋዋሪ ወንጀል ችሎት ቀርቦ ክሱ የደረሰውና በንባብ እንዲሰማ ከተደረገ በኋላ በክሱ ዝርዝሩ ላይ የተጠቀሰውን የወንጀል ድርጊት አለመፈጸሙን ጠቅሶ የዕምነት ክህደት ቃሉን ሰጥቷል፡፡
ከሳሽ ዐቃቤ ህግ ወንጀሉን ያስረዱልኛል ያላቸውን ምስክሮች ዝርዝር ጠቅሶና አቅርቦ የምስክር ጭብጥ በማስመዝገብ የምስክርነት ቃላቸውን በችሎት አሰምቷል፡፡
ፍርድ ቤቱም የዐቃቤ ህግ ማስረጃን መርምሮ የወንጀል ድርጊት መፈጸሙን ማረጋገጡን ጠቅሶ ተከሳሹ በተከሰሰበት ድንጋጌ ስር እንዲከላከል በሰጠው ብይን መሰረት ተከሳሹ የመከላከያ ማስረጃ አቅርቧል።
ተዘዋዋሪ ችሎቱ ተከሳሹ ያቀረበውን የመከላከያ ማስረጃን ከዐቃቤ ህግ ማስረጃ ጋር አመዛዝኖና መርምሮ ተከሳሹ የዐቃቤ ህግ ማስረጃን መከላከል አለመቻሉን ጠቅሶ የጥፋተኝነት ፍርድ አስተላልፎበታል።
ከዚህም በኋላ ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኝ የቅጣት አስተያየት በመመርመርና የተከሳሹን የቅጣት ማቅለያ አስተያየቶችን በመያዝ ተከሳሹን በ3 ዓመት ከ3 ወር ጽኑ እስራትና በ1 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጣ በዛሬው የችሎት ቀጠሮ ውሳኔ ሰጥቷል።
በታሪክ አዱኛ