Fana: At a Speed of Life!

ከሀገር የሸሸ ገንዘብን ለማስመለስ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑ ተገለፀ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 8፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ከሀገር በተለያዩ መንገዶች የሸሸን ሃብት ለማስመለስ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን ጠቅላይ ዓቃቢ ህግ አስታወቀ፡፡

ባለፉት አመታት ከሀገሪቱ በተለያየ መንገድ በርካታ ሃብት ተመዝብሮ ወደ ውጭ ሸሽቷል።

ሃብቱ ሊሸሽ የቻለውም በመንግስት መዋቅር ውስጥ በነበሩና ከእነሱ ጋር ጥብቅ ቁርኝት በነበራቸው ባለሃብቶች ትብብር እንደነበረ ይገለፃል።

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ዓቃቢ ህግ አቶ ብርሁኑ ጸጋዬ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የ2011 ዓ.ም የ11 ወራት የስራ አፈጻጸምን ሪፖርትን ሲያቀርቡ የሸሸውን ሃብት ለማስመለስ ከተወሰኑ ሀገራት ጋር ስምምነት ላይ መደረሱን ገልፀዋል፡፡

እንዲሁም ከሌሎች ሀገራት ጋር ሃብቱን ለማስመለስ በጥንካሬ እየተሰራ መሆኑን ገልጸው ነበር ።

ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትም ይህ የተመዘበረውን ሃብት የማስመለስ ሂደት ምን ደረጃ ላይ ይገኛል ሲል ጠይቋል።

ሃብቱ የተደበቀው በእነማን እና የት እንደሆነ ተልይቷል ያሉት በጠቅላይ ዓቃቢ ህግ የህዝብ ግንኙነት ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ዝናቡ ቱሉ፥ በወንጀል የተገኘ ሃብትን የማስተዳደር ስርዓት አለመኖሩ በሂደቱ ችግር መፍጠሩን አንስተዋል፡፡

ዳይሬክተሩ አሁን ላይ ሃብት የማስመለስ ዳይሬክቶሬት መቋቋሙን በመግለፅ÷ በዚህ የተሳተፉ ወንጀለኞች በህግ እንዲጠየቁ ማድረጉ በትኩረት እየተሰራበት ነው ብለዋል።

ጉዳዩ ውስብስብና ጊዜ የሚጠይቅ መሆኑን ያነሱት አቶ ዝናቡ፥ የምራመራ ሂደቱ ሲጠናቀቅ በእነማን እና የት ሀገር ሃብት ሸሸ የሚለው ወደ ፊት ይፋ እንደሚደረግ ተናግረዋል፡፡

ከዚህ ባለፈም በሀገሪቱ በወንጀልና በሙስና የተዘረፈን የሀገርና የህዝብ ሃብት የማስመለሱ ስራ መጠናከሩን አቶ ዝናቡ ጠቁመዋል፡፡

በ2011 ዓ.ም ያለአግባብ የህዝብ ሃብትን ለራሳቸው አድርገው ያከማቹትን በማጣራትና በመለየት ከ95 ሚሊየን ብር በላይ ማስመለስ እንደተቻለ የተናገሩት ዳይሬክተሩ፥ ባለፉት ሶስት ወራትም ከ35 ሚሊየን ብር በላይ ማስመለስ ተችሏል ነው ያሉት ።

በጌታሰው የሽዋስ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.