ስፓርት

በስፖርታዊ ጨዋታዎች እና ውድድሮች የአደረጃጀት እና የአሠራር ረቂቅ መመሪያ ላይ ውይይት ተካሄደ

By Meseret Demissu

September 03, 2020

አዲስ አበባ ፣ ነሀሴ 28 ፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ)በስፖርታዊ ጨዋታዎች እና ውድድሮች የአደረጃጀት እና የአሠራር ረቂቅመመሪያ ላይ ውይይት ተካሂዷል።

በኢትዮጵያ በተለያየ ደረጃ የተለያዩ ውድድሮች እና ጨዋታዎች የሚዘጋጁ ሲሆን ÷የሚዘጋጁት ውድድሮች በተደራሽነት ፣ በጥራት ፣በውጤት እና በፍትሐዊነት ደረጃ ጉድለቶች ያሉባቸው መሆኑን የስፖርት ሪፎርም ጥናቱ ማመላከቱ ተገልጿል፡፡

በተለይም በኢትዮጵያ ሚዘጋጁ ውድድሮች የጥራት ደረጃ እና በአህጉር እና ዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚዘጋጁ ውድድሮች ጋር ያለው ተመጋጋቢነት ክፍተት ያለበት መሆኑ  ተጠቅሷል።

ከዚያም ባለፈ ለአዲስ እና ተተኪ ስፖርተኞች የሚሰጠው ዕድል አናሳ በመሆኑ  በሚፈለገው ደረጃ  ውጤታማ መሆን አለመቻሉን  ጥናቱ አመላክቷል ፡፡

በመሆኑም የሪፎርም ጥናቱን ምክረ ሀሳብ መነሻ በማድረግ በሀገራችን የሚዘጋጁ ውድድሮች ደረጃቸውን የጠበቁ እና በአህጉር እና ዓለም ዓቀፍ ደረጃ ከሚዘጋጁ ውድድሮች ጋር ተመጋጋቢ እና ውጤታማ ለማድረግ በአሠራር ማስደገፍ ተገቢ በመሆኑ  የውድድሮች አደረጃጀት እና የአሠራር መመሪያ እንዲዘጋጅ  ማስፈለጉ ተገልጿል ፡፡

በተዘጋጀው ረቂቅ መመሪያ ዙሪያም  ዛሬ ከሀገር አቀፍ ስፖርት ማህበራት እና ከታወቁ የስፖርት ድርጅቶች ጋር ውይይት በማድረግ ግብዓት ተሰብስቧል ፡፡

ከዚህ በተጨማሪም የማህበረሰብ ስፖርት ተሳትፎን ለማሳደግ እና ለማስፋፋት የሚያስችል ሰነድ ላይ ውይይት መካሄዱን ከኢፌዲሪ ስፖርት ኮሚሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡