የሀገር ውስጥ ዜና

የመኪና መስታወት በመስበር 600 ሺህ ብር ሰርቀው ለመሰወር የሞከሩ ተጠርጣሪዎች ተያዙ

By Tibebu Kebede

December 24, 2019

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 14፣ 2012(ኤፍቢሲ) አቶ ሙዲን ከድር  የተባሉ ግለሰብ በእቁብ ያጠራቀሙትን   600 ሺህ  ብር የመኪና መስታወት በመስበር  ሰርቀው ለመሰወር የሞከሩ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ዋሉ።

ተጠርጣሪዎች  ድርጊቱን ሲፈፅሙ  ባያቸው የሞተር ሳይክል አሽከርከሪ ትብብር እና በፖሊስ አባላት ክትትል ወዲያውኑ መያዛቸውን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን  አስታውቋል፡፡

ጉዳዩን የሚከታተሉት ዋና ሳጅን ደነቀው አየነው በተያዙት 3 ተጠርጣሪዎች ላይ ምርመራ እየተደረገባቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡

ለህብረተሰቡ ባስተላለፉት መልዕክት ግለሰቦች ከፍተኛ ቁጥር ያለውን ገንዘብ ይዞ ከመንቀሳቀስ ይልቅ በባንክ አገልግሎቶች መጠቀምን እንደባህል መልመድ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ህብረተሰቡና ፖሊስ በተጠናከረ ትስስር ከሠሩ ወንጀልን ፈፅሞ ከህግ እንደማያመልጥ ያስመሠከረ ስራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹን እስከ መጨረሻ ተከታትለው በቁጥጥር ሥር ያዋሉትን የሞተር ሣይክል አሽከርካሪና የፖሊስ አባላትን ዋና ሳጅኑ አመስግነዋል፡፡