የሀገር ውስጥ ዜና

በቴሌኮም ዘርፍ የማሻሻያ ስራዎች ሂደት ላይ ያተኮረ ውይይት በጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ተካሄደ

By Tibebu Kebede

October 26, 2020

አዲስ አበባ ፣ ጥቅምት 16 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በቴሌኮም ዘርፍ የማሻሻያ ስራዎች ሂደት ላይ ያተኮረ ውይይት በጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ተካሄዷል፡፡

አዳዲስ የቴሌኮም ኦፕሬተሮችን ወደሃገር ውስጥ በማስገባት ዘርፉን ለውድድር ክፍት ለማድረግ እና የኢትዮ ቴሌኮምን ድርሻ በከፊል ለማዛወር እስካሁን የተሰሩ ስራዎች በውይይቱ ሪፖርት ቀርቧል፡፡

በዘርፉ የሚደረገው ማሻሻያ ብሄራዊ ጥቅምን ያስጠበቀ እና የሚፈለገውን ውጤት የሚያመጣ እንዲሆን ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ምክክር መካሄዱ ተገልጿል፡፡

ከዚህ ቀደም በተካሄዱ ውይይቶች የተነሱ ጥያቄዎችና የቀረቡ ምክረ ሃሳቦችን በመመልከት የሪፎርም ስራው እንዲቀጥል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አቅጣጫ አስቀምጠዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሂደቱ የሚሳተፍ የትኛውም አካል ከሚደረገው ቁጥጥር ባሻገር ራሱን ከሌብነት ሊያጸዳ ይገባልም ብለዋል፡፡

ከዚህ በፊት በዘርፉ ዙሪያ የገንዘብ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ኮሙዩኒኬሽን ባለስልጣን እና ኢትዮ ቴሌኮም ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላትና ምሁራን ጋር ውይይት ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡

በአላዛር ታደለ