የሀገር ውስጥ ዜና

በትግራይ ክልል የሐሰት ፕሮፓጋንዳ በሚነዙ መገናኛ ብዙኀን ላይ እርምጃ ሊወሰድ ይገባል – አፈ ጉባኤ አደም ፋራህ

By Abrham Fekede

November 08, 2020

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 29፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በትግራይ ክልል የሐሰት ፕሮፓጋንዳ የሚነዙና በህዝቡ ውስጥ ውዥንብር የሚፈጥሩ መገናኛ ብዙኀን ላይ እርምጃ እንዲወሰድ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አሳሰበ።

የምክር ቤቱ አፈ-ጉባኤ አደም ፋራህ በክልሉ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በመጠቀም ከህገ-መንግሥቱ ጋር በሚቃረን መልኩ ሁከትና ብጥብጥ እንዲፈጠርና አገር እንዲተራመስ በሚሰሩ መገናኛ ብዙኀን ላይ ቁጥጥር እንዲደረግም ጥሪ አቅርበዋል።

አፈ ጉባኤው “ህገ-መንግሥታዊ መብት በሚጥስ መልኩ በሚንቀሳቀስ የመገናኛ ብዙኀን ተቋም ላይ ተገቢ እርምጃ ሊወሰድ ይገባልም” ብለዋል።

ሥልጣን የተሰጣቸው ተቋማት ህገ-መንግሥቱንና መገናኛ ብዙኀን አስመልክቶ የወጡ ህጎች አፈጻጸምን በመከታተል ጥሰት በሚፈጽሙ አካላት ላይ ህጋዊ እርምጃ እንዲወስዱ ነው ያሳሰቡት።

አፈጉባኤው በህገ-መንግሥቱ መሠረት የፌዴሬሽን ምክር ቤት በመፈቃቀድና በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ሕብረ ብሔራዊ አንድነት እንዲዳብር ይሠራል ነው ያሉት።

ይህንን ተፈጻሚ ለማድረግ የትምህርት ተቋማትና መገናኛ ብዙኀን ትልቅ ኃላፊነት እንዳለባቸው መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

አፈ-ጉባኤው መገናኛ ብዙኀን የጋራ ማንነት ለመፍጠር መሥራት እንደሚገባቸው ጠቁመው፣ ከዚህ በተቃራኒ የሚሰሩ ካሉ ተገቢ እርምጃ ሊወሰድባቸው እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት።