Fana: At a Speed of Life!

የአዲስ አበባ ውሃ ሃብት እንክብካቤን ለማሻሻል ከ9 ነጥብ 3 ሚሊየን ዩሮ በላይ ስምምነት ተፈረመ

አዲስ አበባ፣ ህዳር 4፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ከቪተንስ ኢቪደስ ኢንተርናሽናል ከተባለ መንግስታዊ ካልሆነ ድርጅት ጋር የአዲስ አበባ ውሃ ሃብት እንክብካቤን ለማሻሻል የሚያግዝ ከ9 ነጥብ 3 ሚሊየን ዩሮ በላይ ስምምነት ተፈራረመ፡፡
በስምምነቱ መሰረትም በድሬ እና ለገዳዲ ተፋሰሶች ለሚኖሩ ነዋሪዎች የውሃ እና የንፅህና አጠባበቅ አቅርቦትን የማሻሻል ስራ ይሰራል ነው የተባለው፡፡
በስምምነቱ በዕቅድ ከተያዙ ተግባራት መካከል በተፋሰስ ልማት እና አጠቃቀም ላይ በአዲስ አበባ፣ በኦሮሚያ ክልል እና በፌደራል ተቋማት መካከል የክልል ተሻጋሪ ውይይትን ማጎልበት፣ የለገዳዲ እና ድሬ የግድቦችን ውሃ የመያዝ አቅም ዘላቂነት ማሻሻል፣ የግድብ የውሃ ጥራትን ማስጠበቅ እንዲሁም የደለል መጠንን በመቀነስ ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
በተጨማሪም በድሬ እና በገዳዲ ግድቦች ተፋሰስ ኣካባቢ ለሚኖሩ ሰዎች ገበያ ተኮር የኑሮ ማሻሻያ ዕድሎችን በመፍጠር እና የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን በማበረታታት የምግብ ዋስትናን በዘላቂነት የማሳደግ ስራ እንደሚገኙበት ተጠቅሷል፡፡
በፕሮጀክቱም በእነዚህ የውሃ ተፋሰስ ውስጥ እና በዙሪያዋ የሚገኙ የአቃቂ፣ ቡራዩ፣ ገላን፣ ሱሉልታ እና ሰንዳፋ የሚኖሩ 90 ሺህ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው ተብሏል፡፡
ፕሮጀክቱም በአምስት ዓመታት ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ ከአዲስ አበባ ውሃ እና ፍሳሽ ባለስልጣን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
የድሬ ተፋሰስን በኢትዮጵያ የኔዘርላንድ ምክትል አምባሳደር፣ የአዲስ አበባ ውሃ እና ፍሳሽ ባለስልጣን ፣ በቪቴንስ ኢቪደስ ኢንተርናሽናል አመራሮች እና የሚመለከታቸው አካላት ጉብኝተዋል፡፡
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.