የሀገር ውስጥ ዜና

አምባሳደር ዘነቡ ታደሰ ከአውሮፓ ህብረት ፓርላማ የሮም ላይዘን ኦፊስ ሊቀመንበር ጋር ተወያዩ

By Tibebu Kebede

December 08, 2020

አዲስ አበባ ፣ ህዳር 29 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በጣሊያን የኢትዮጵያ አምባሳደር ዘነቡ ታደሰ ከአውሮፓ ህብረት ፓርላማ የሮም ላይዘን ፅህፈት ቤት ሊቀመንበር ካርሎ ኮራዛ ጋር በወቅታዊ የኢትዮጵያ ጉዳዮች ላይ ተወያዩ።

በውይይቱ አምባሳደሯ ከለውጡ በኋላ ኢትዮጵያ እየሄደችበት ያለውን አጠቃላይ የለውጥ ሂደት፣ ሴረኛው ህወሓት ከለውጡ በተቃራኒ ያቅድ እና ያደርስ የነበረውን ጥፋት፣ መንግስት ከህወሓት ጁንታ ጋር የነበረውን ልዩነት በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የሄደበትን ርቀት እንዲሁም ጁንታው በመከላከያ ሰራዊቱ እና በሰላማዊ ዜጎች ላይ ያደረሰውን አረመኔያዊ ጥቃት በተመለከተ ለሊቀ መንበሩ ገለፃ አድርገውላቸዋል።

ሊቀ መንበሩ በበኩላቸው መንግሥት ጥረት እያደረገ ያለው ህግ ለማስከበርና ይህን አሳዛኝ ድርጊት ለመግታት እንደሆነ መረዳታቸውንና ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሰላምን ለማስፈን እየሠሩ መሆኑን እንደተረዱ ገልጸዋል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ በኩል ድጋፍ ማድረግ በሚያስፈልግ ነገር ሁሉ ለመደገፍ ዝግጁ መሆናቸውን መግለፃቸውን ከኤምባሲው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

አምባሳደሯ መንግሥት የወሰደው እርምጃ ህግና ህገ-መንግሥታዊ ሥርዓትን ማስከበር፣ ወንጀለኞችን ለህግ የማቅረብ ሥራ እንደሆነ እና ጉዳዩም የውስጥ ጉዳይ በመሆኑ ማንም በዚህ ጉዳይ ላይ ጣልቃ መግባት ወይም በሂደቱ ላይ ጫና ማሳረፍ እንደሌለበት አውስተዋል፡፡ የተፈናቀሉ ሰዎችን በተመለከተ መንግስት ከአሁን በፊት ከለውጡ ማግስት በህወሓት እኩይ ተግባር ተፈናቅለው የነበሩ በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎችን መልሶ ማቋቋም መቻሉን ገልፀው አሁንም የተፈናቀሉትን ለመመለስ እና ለማቋቋም ኮሚቴ አዋቅሮ እየሰራ መሆኑን እና ልምዱም እንዳለው በማስረዳት በዚህ ረገድ የህብረቱ ሰብዓዊ ድጋፍ ላይ ማተኮር እንዳለበት አንስተዋል።

ኮቪድ-19፣ በተለያዩ ቦታዎች የተከሰተው ጎርፍ፣ አሁንም ድረስ እንደገና እየተከሰተ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ባለው የአንበጣ መንጋ ምክንያት በኢትዮጵያ የግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ ስለተጎዳ መንግስት ገበሬውን በመስኖ እና ሌሎች እንቅስቃሴዎች አግዞ ራሱን ለማስቻል በሚያደርገው ጥረት ህብረቱ የሚሰጠውን የፋይናንስ እና ቴክኒከ ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥል አስፈላጊው ድጋፍ እንዲደረግ እንደሚፈልጉም አስረድተዋል።