የሀገር ውስጥ ዜና

የደብረ ብርሃን ኢንዱስትሪ ፓርክን ጨምሮ በአማራ ክልል የሚገኙ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን መደገፍ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይት ተካሄደ

By Tibebu Kebede

December 31, 2020

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 22፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የደብረ ብርሃን ኢንዱስትሪ ፓርክን ጨምሮ ሌሎች በአማራ ክልል የሚገኙ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በቅርበት መደገፍ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ውይይት ተካሄደ።

በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ፋንታ ማንደፍሮ የተመራ የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስ ልዑክ በደብረ ብርሀን ኢንዱስትሪ ፓርክ በመገኘት የመስክ ጉብኝት እና በተለያዩ ጉዳዩች ላይ ውይይት አድርጓል።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሳንዶካን ደበበን ጨምሮ ሌሎች የስራ ሀላፊዎች እንዲሁም ሚኒስትር ዲኤታዎች፣ የክልል፣ የዞን እና የከተማ አስተዳደር አመራሮች ከህብረተሰቡ ከተውጣጡ ተወካዩች ጋር ውይይት አድርገዋል።

በውይይቱም የኮርፖሬሽኑ ምክትል ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሽፈራው ሰለሞን ስለ ኮርፖሬሽኑ እና በክልሉ ስለገነባቸው የኢንዱስትሪ ፓርኮች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

ውይይቱ በዋናነት የደብረብርሃን ኢንዱስትሪ ፓርክን ጨምሮ ሌሎች በክልሉ የሚገኙ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በቅርበት መደገፍ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ መሆኑን ከኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ያገኘነው መረጃ ያሳያል።

ከፓርኮች ጋር የተያያዙ የወሰን ማስከበር ችግሮች፣ ለኢንዱስትሪ ፓርኮች የሰራተኞች አቅርቦት፣ የጸጥታና ደህነት ጉዳዮች፣ የጤና ማዕከላትን ስለማጠናከር፣ ለልማት ተነሽውች ስለሚደረግ ዘለቄታዊ ድጋፍ፣ የተጀመሩ የመንገድ ስራዎችን ማጠናቀቅ ስለሚቻልባቸው ሁኔታዎች፣ ስለ ሰራተኞች የመኖሪያ ቤት አቅርቦች እና ሌሎች አንኳር ጉዳዮች ላይ መክረዋል፡፡

በመድረኩም ከተሳታፊዎች የተለያዩ አስተያየቶች እና ጥያቄዎች የተነሱ ሲሆን ምክትል ርእሰ መስተዳድሩ፣ በዋና ስራ አስፈጻሚው፣ በሚኒስቴር ዲኤታዎች እና በሌሎች የመንግስት የስራ ሃላፊዎች ምላሽ እና ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ በቀጥታ ከ74 ሺህ በላይ እንዲሁም ቀጥተኛ ባልሆነ መንገድ ከ186 ሺህ በላይ ለሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፈጠሩ ተገልጿል፡፡

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤ ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!