የሀገር ውስጥ ዜና

የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ህልውና ለመጠበቅ በተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ ላይ ሁሉም አካል ርብርብ ሊያደርግ እንደሚገባ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሳሰቡ

By Meseret Awoke

January 03, 2021

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 25፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ህልውና ለመጠበቅ በተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ ላይ ሁሉም አካል ርብርብ ሊያደርግ እንደሚገባ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አገኘሁ ተሻገር አሳሰቡ፡፡

የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ የ2013 ዓ.ም የበጋ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ እንዲሁም ያለፉትን ዓመታት የሥራ ክንውን እውቅና የሚሰጥበት የንቅናቄ መድረክ በባሕር ዳር እያካሄደ ነው፡፡

በመድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አገኘሁ ተሻገር ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከመገንባት ባሻገር ለህልውናውም ማሰብ ተገቢ ነው ብለዋል፡፡

ግድቡ በደለል እንዳይሞላ የተፈጥሩ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራን በጥራትና በስፋት ማካሄድ እንደሚገባም ርዕሰ መስተዳድሩ አስገንዝበዋል፡፡

በእንቦጭ አረም ምክንያት አደጋ ላይ የወደቀዉን ጣና ሐይቅ ለመታደግ አረሙን ነቅሎ ማስወገድ ብቻ መፍትሄ ባለመሆኑ በደለል እንዳይሞላ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ በየአካባቢው ማከናወን ይገባል ብለዋል፡፡

የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ኀላፊ ዶክተር መለሰ መኮንን በዘንድሮው የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ የሚሳተፉ አካላት ሥራዉ ዘላቂ እዲሆን በባለቤትነት ትኩረት ሰጥተው እንዲሠሩ መጠየቃቸውን አብመድ ዘግቧል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤ ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!