የሀገር ውስጥ ዜና

የመተከል ዞን አመራሮች የአቅም ግንባታ ስልጠና እየተሰጠ ነው

By Tibebu Kebede

January 11, 2021

አዲስ አበባ ፣ ጥር 3 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የመተከል ዞንና ወረዳ ነባርና አዳዲስ አመራሮች የአቅም ግንባታ ስልጠና እየተሰጠ ነው።

ዓለም አቀፋዊ፣ አህጉራዊ፣ ሀገራዊና ክልላዊ ይዘቶች ያሉትና በቪዲዮ ተቀርፆ የቀረበው የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ መልዕክትም ለሰልጣኞቹ ቀርቧል።

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ብልፅግና ፓርቲ የስልጠና እና ሱፐር ቪዥን ዘርፍ ሃላፊ አቶ አንዳርጋቸው ሞላ እንዳሉት በስልጠናው የመተከል ዞንና ወረዳ ነባርና ተተኪ አመራሮች ተሳትፈዋል።

የስልጠናው ዋነኛ አላማ በዞኑ የሚታዩ የፀጥታ ችግሮችንና አጠቃላይ የአመራር ብቃት ክፍተቶችን ለመሙላት መሆኑንም ገልጸዋል።

ኢዜአ ያነጋገራቸው አመራሮችም ከስልጠናው የተሻለ ግንዛቤ እንደሚያገኙ ተናግረዋል።

ስልጠናው በዞኑ የሚታየውን የፀጥታ ችግር ለመፍታት እንደ አንድ መፍትሄ ይታያል ያሉት አቶ አንዳርጋቸው፣ በተለይ አሁን እየመጡ ያሉ ተተኪ አመራሮች በህዝብ ይሁንታና ግምገማ የመጡ መሆናቸው ለአካባቢው መረጋጋት አስተዋፅኦ እንዳለው ተናግረዋል።