የሀገር ውስጥ ዜና

በሶማሌ ክልል የኢንቨስትመንት እና ዳያስፖራ ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ የተመራ ልዑክ ከጂቡቲ ባለሀብቶች ጋር ተወያየ

By Tibebu Kebede

January 12, 2021

አዲስ አበባ ፣ ጥር 4 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በሶማሌ ክልል የኢንቨስትመንት እና ዳያስፖራ ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ የተመራ የክልሉ የስራ ሀላፊዎች ልዑክ ከጂቡቲ ባለሀብቶች ጋር በጂቡቲ ከተማ ተወያየ።

በሶማሌ ክልል የኢንቨስትመንት እና ዳያስፖራ ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱልሰላም የሱፍ፣ የኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ምክትል ሀላፊ አቶ ጅምዓሌ አህመድ እና የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ቢሮ ምክትል ሀላፊ አቶ ሀሰን ቡልቡል ከጂቡቲ ባለሀብቶች ጋር በኢትዮጵያ እና በሶማሌ ክልል ያሉ የኢንቨስትመንት አማራጮች ዙሪያ ከባለሀብቶች ጋር ተወያይተዋል።

በውይይቱም አቶ አብዱልሰላም የሱፍ በሶማሌ ክልል ያለው አስተማማኝ ሰላም ክልሉን ለኢንቨስትመንት ምቹ እንደሚያርገው ገልጸዋል።

የጂቡቲ ባለሀብቶችም በኢትዮጵያ ያሉ የኢንቨስትመንት አማራጮችን በማየት መዋዕለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ ጥሪ አቅርበዋል።

ባለሀብቶቹ በበኩላቸው በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸው፥ በተለይም የሶማሌ ክልልና ሌሎች አካባቢዎችን እንደሚመለከቱ አስታውቀዋል።

ከውይይቱ በኋላ የጂቡቲ ባለሀብቶችን ያካተተ ልዑክ ከሁለት ሳምንት በኋላ ወደ ሶማሌ ክልል እንደሚመጣና በክልሉ ያለውን የኢንቨስትመንት አማራጭ እንደሚመለከት ከሶማሌ ክልል መንግስት ኮሙዩኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤ ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!