አምባሳደር አለማየሁ ተገኑ ከሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ መምሪያ ምክትል ዳይሬክተር ጋር ተወያዩ

By Tibebu Kebede

January 15, 2021

አዲስ አበባ ፣ ጥር 7 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በሩሲያ የኢፌዴሪ ባለ ሙሉ ሥልጣን አምባሳደር አለማየሁ ተገኑ ከሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ መምሪያ ምክትል ዳይሬክተር ቶዶ ጆርጂ ቭላዲሚሮቪች ጋር ተወያዩ።

ውይይቱ በዋናነት የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ እና የሁለቱን ሃገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ላይ ያተኮረ ነበር ፡፡

አምባሳደር አለማየሁ ወቅታዊ የኢትዮጵያን ሁኔታ በሚመለከት በትግራይ ክልል የተካሄደው የህግ የበላይነት የማስከበር ዘመቻ በተሳካ ሁኔታ ተካሂዶ መጠናቀቁን ገልፀዋል።

ከዚህ ባለፈም በህግ የሚፈለጉ የህወሓት ጁንታ ቡድን አባላትን በህግ ቁጥጥር ሥር ለማዋል ከሚደረገው ጥረት ጎን ለጎን፣ የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦትን ማዳረስ፣ ጁንታው ያፈረሰውን መሰረተ ልማት መልሶ ግንባታ እና ዜጎችን መልሶ የማቋቋም ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ አስረድተዋል።

በተጨማሪም በክልሉ የተቋቋመው ጊዜያዊ አስተዳደር በየደረጃው ያሉትን መዋቅሮች መልሶ የማደራጀት፣ ከህዝብ ጋር ውይይቶችን በማድረግ መረጋጋት ለማስፈን እየሰራ እንደሚገኝም አብራርተዋል።

በክልሉ የመሰረተ ልማት ግንባታ እንደገና እንዲመለሱ ተደርጓል ያሉት አምባሳደሩ ህይወት ቀስ በቀስ ወደ መደበኛ ሁኔታ እየተመለሰች መሆኗንም አውስተዋል።

የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ መምሪያ ምክትል ዳይሬክተር ቶዶ ጆርጂ ቭላዲሚሮቪች በበኩላቸው በትግራይ ክልል የሕግ የበላይነት የማስከበር ሥራ የሃገሪቱ ውስጣዊ ጉዳይ በመሆኑ ጣልገብነት እንደማያስፈልግ ጠቅሰዋል፡፡

ከሱዳን ጋር ስላለው የድንበር ውዝግብ ጉዳይ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ መፍትሄ እንደሚያገኝ ያላቸውን ተስፋ መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጽህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤ ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!