የሀገር ውስጥ ዜና

ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን  የከተራና የጥምቀት በዓል ያለ ምንም የፀጥታ ችግር በሰላም እንዲከበር ዝግጅት ማጠናቀቁን ገለፀ

By Tibebu Kebede

January 16, 2021

አዲስ አበባ ፣ ጥር 8 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ)በመላው ኢትዮጵያ በታላቅ ድምቀት የሚከበረው የከተራና የጥምቀት በዓል ያለ ምንም የፀጥታ ችግር በሰላም እንዲከበር የፌዴራል፣ የክልል፣ የአዲስ አበባና የድሬደዋ ፖሊስ ኮሚሽኖች እንዲሁም የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት እና ሌሎች የጸጥታና የፍትህ አካላት በቂ ዝግጅት በማድረግ ተቀናጅተው እየሰሩ መሆናቸውን የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አስታውቋል፡፡

በሃገሪቱ በየዓመቱ የሚከበረው የከተራና የጥምቀት በዓል ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ በዩኒስኮ ካስመዘገበቻቸው የማይደሰሱ ቅርሶች ውስጥ አንደኛው መሆኑን ኮሚሽኑ አስታውሷል፡፡

ይህ ታላቅ በዓል በመላው ኢትዮጵያ በታላቅ ድምቀት የሚከበር ሀይማኖታዊ በዓል ከመሆኑም በላይ የቱሪስት መስህብ በመሆን የሃገሪቱን መልካም ገፅታ በመገንባት ረገድ ጉልህ ሚና አለው ብሏል፡፡

በመሆኑም በመላው ሀገሪቱ በታላቅ ድምቀት የሚከበረው የከተራና የጥምቀት በዓል ያለ ምንም የፀጥታ ችግር በሰላም እንዲከበር የፌዴራል፣ የክልል፣ የአዲስ አበባና የድሬደዋ ፖሊስ ኮሚሽኖች እንዲሁም የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት እና ሌሎች የጸጥታና የፍትህ አካላት በቂ ዝግጅት በማድረግ ተቀናጅተው እየሰሩ መሆናቸውን የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አስታውቋል፡፡

ኮሚሽኑ መላውን ሰላም ወዳድ የሀገሪቱ ህዝቦች ከጎኑ በማሰለፍ የከተራ እና የጥምቀት በዓል ያለምንም የፀጥታ ችግር በሰላም እንዲከበር ለማድረግ በሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎች በርካታ የፀጥታ አካላት ማሰማራቱን ገልጿል።

በታቦታት ማደሪያ ስፍራዎችና በርካታ የበዓሉ ታዳሚዎች በሚገኙበት አካባቢ ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ ፖሊሳዊ አገልግሎት የሚሰጥ መሆኑን ገልጿል፡፡

በበዓሉ ሂደት ርችት መተኮስ ለፀረ-ሰላም ኃይሎች ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር በመሆኑ ፍፁም የተከለከለ መሆኑን ኮሚሽኑ አስታውቆ በዓሉ በሚከበርበት ስፍራም ምንም አይነት የጦር መሳሪያ፣ ተቀጣጣይም ሆነ ስለታማ ቁሳቁስ ይዞ መንቀሳቀስ የማይቻል እንደሆነና ለሁሉም ደህንነት ሲባል ፍተሻ የሚደረግ መሆኑን የበዓሉ ታዳሚዎች ተረድተው ትብብር እንዲያደርጉ ኮሚሽኑ አሳስቧል።

በሌላ በኩል ፖሊስ ከህብረተሰቡ ባገኘው መረጃ መሰረት በዓሉ በሰላም እንዳይጠናቀቅ የተለያዩ የግል አጀንዳዎችን አንግበው የበዓሉን ስነ-ስርዓት ለማወክ ግጭት ለማስናሳትና ሌሎች አደጋዎችንም ለማድረስ የተዘጋጁ አንዳንድ ፀረ-ሰላም ኃይሎች እንዳሉ እንደደረሰበት አስታውቋል፡፡

ስለሆነም የሰላሙ ባለቤት የሆነው መላው ህዝብ ይህንን ተገንዝቦ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርግ እንደሚገባና አጠራጣሪ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙት በፍጥነት የፖሊስ አገልግሎት ለማግኘት ወይም ጥቆማ ለመስጠት በስልክ ቁጥር ÷

0115-52-63-03፣ 0115-52-40-77፣ 0115-54-36-78 እና 0115-54-36-81 እንዲሁም በ987 እና 816 ነፃ የስልክ መስመሮች መጠቀም እንደሚችል በተጨማሪም በአካባቢው ላለ የፀጥታ ሀይል መረጃውን በአካል ማድረስ እንደሚችል ኮሚሽኑ ጠቁሟል፡፡