ቴክ

ዋርነር ብሮስ በቦክስ ኦፊስ ቀዳሚ መሆን የሚችሉትን ፊልሞች በሰው ሰራሽ መሳሪያ መገመት ሊጀምር ነው

By Tibebu Kebede

January 10, 2020

አዲስ አበባ፣ ጥር 1፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የሆሊውዱ የፊልም ኩባንያ ዋርነር ብሮስ የቦክስ ኦፊስን የደረጃ ሰንጠረዥ በሰው ሰራሽ መሳሪያ (አርቴፊሻል ኢንተሌጀንስ) መገመት ሊጀምር መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

ሰው ሰራሽ መሳሪያው ዋርነር ብሮስ የሚያዘጋጃቸው ፊልሞች ምን ያህል ስኬታማ ሊሆኑ እንደሚችሉ ግምቱን ያስቀምጣል ተብሏል፡፡

ይህ አሰራር የተዋናይ አመራረጥን፣ የማከፋፈሉን ሂደት እና የሚለቀቅበትን ጊዜ መነሻ በማድረግ ትርፋማነቱን ይገመግማል ነው የተባለው፡፡

በሆሊውድ መንደር ከስድስት ትልልቅ የፊልም ኩባንያዎች አንዱ የሆነው ዋርነር ብሮስ ይህን አሰራር ተግባራዊ ለማድረግ ከኤልኤ ስታርት አፕ ሲኔለይቲክ ጋር ስምምነት ተፈራርሟል፡፡

የመገመቻ መሳሪያው ባለፈው ዓመት ይፋ የሆነ ሲሆን ለዘርፉ አዲስ ይዘት እና አሰራርን ይዞ መምጣቱ ሲኔለይቲክ በድረ ገፁ አስነብቧል፡፡

መሳሪያው የተለያዩ መረጃዎችን በመጠቀም የቦክስ ኦፊስ የደረጃ ሰንጠረዥን በትክክል እንደሚገምት ተጠቁሟል፡፡

አንዱ የዚህ መሳሪያ አገልግሎት ተጠቃሚዎች ተዋንያን የሚመርጡበት ሂደት እንዴት በፊልሙ ትርፋማነት ላይ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር መመልከት እንዲችሉ ያደርጋል ነው የተባለው፡፡

ምንጭ፡-ስካይ ኒውስ