Fana: At a Speed of Life!

ባለስልጣኑ ሉዓላዊነት እና አብሮነትን በሚፈታተኑ ሚዲያዎች ላይ እርምጃ እንደሚወስድ አስታወቀ

አዲስ አበባ ፣ መጋቢት 6 ፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን  ሉዓላዊነት እና አብሮነትን የሚፈታተኑ ሚዲያዎች ላይ እርምጃ እንደሚወስድ አስታወቀ።

የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ወንድወሰን አንዷለም ÷በትግራይ ክልል የተካሄደውን የህግ ማስከበር ዘመቻ ተከትሎ በትግራይ ክልል የተፈጠሩ ክስተቶችን አንዳንድ የውጭ መገናኛ ብዙኃን በአድልዎ የተሞላ፣ ሚዛናዊ ያልሆነ፣ የትክክለኛነት ችግር ያለበት፣ በተለያዩ ፍላጎቶች የተተበተበ እና የተለየ ተልዕኮ ያነገቡ ዜናዎችን፣ ዘጋቢ ፊልሞችን እና ሌሎች ዘገባዎችን እየሰሩ እንደሆነ የሚዲያ ሞኒተሪንግ የሁኔታ ግምገማ ያመላክታል ብለዋል።

አንዳንድ ዓለም አቀፍ ሚዲያ ተቋማት የሰሯቸው ዘገባዎች በአጠቃላይ የጋዜጠኝነት ሙያ አስተምህሮቶች እና ሙያዊ የስነ ምግባር ጥያቄዎችን የሚያስነሳ ነው ያሉት አቶ ወንድወሰን ÷ ሥራዎቻቸው በጣም የሚያስተዛዝቡና የሚያበሳጩ ጭምር መሆናቸውን አመልክተዋል።

የተፋለሰ፣ የተዛባና ከራሱ ጭምር የተጣላ የዜና አዘጋገብ የተከተሉበት የተለያዩ ምክንያቶች ሊኖሩ እንደሚችሉ የጠቆሙት ምክትል ዳይሬክተሩ÷ የተፋለሱ እና የተዛቡ ዘገባዎችን የሚሰሩ አንዳንድ ጋዜጠኞች በጥቅም የሚዘወሩ ናቸው ብለዋል።

የተዛቡ ዘገባዎችን ሲያስተላልፉ የነበሩ አንዳንድ ጋዜጠኞች ከዚህ ቀደም በሀገሪቱ ስልጣን ላይ ከነበረው እና ህግ የማስከበር እርምጃ ከተወሰደበት ቡድን መሪዎች እና አጀንዳ አዘጋጆች ጋር ወዳጅነት ያላቸው መሆናቸውን በተጨባጭ ማስረጃ ማረጋገጥ መቻሉንም  ነው የተናገሩት ።

ዓለም አቀፍ ሚዲያ እና ዘገባዎችን የሚሰሩ ባለሙያዎችን ለይቶ ማየት ያስፈልጋል የሚሉት አቶ ወንድወሰን ÷ አንድ የሚዲያ ተቋም የላከው ጋዜጠኛ ስህተት ሰራ ማለት ሚዲያዎቹ ሙሉ በሙሉ ከእውነት፣ ከፍትህ እና ከሀቅ የተፋቱ ናቸው የሚል ድምዳሜ ላይ መድረስ እንደማያስችል አንስተዋል።

የተዛቡ ዘገባዎችን እንዲሰሩ እያደረጋቸው ያለው የመረጃ እጥረት ይሆን የሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ የመረጃ ቅብብል እና እየሆነ ያለውን ነገር በትክክል ከማስተላለፍ አንጻር ችግሩ እንደ ሀገር ያለ ችግር መሆኑን ባይክዱም፤ የውጭ ሚዲያዎች የትግራይን ሁኔታ በተሳከረ መንገድ እንዲዘግቡ ያደረጋቸው የመረጃ እጥረት ነው ብለው እንደማያምኑ ገልጸዋል።

እንደ  ሀላፊው ማብራሪያ ሚዲያዎች በትግራይ ክልል ገብተው ለመዘገብ ጥያቄ ማቅረባቸውን ተከትሎ በስፍራው ሄደው እንዲዘግቡ መንግሥት ፈቅዷል።

መንግሥት ከፈቀደ በኋላ ወደ ክልሉ የገቡ ጋዜጠኞች ሚዛናዊነት የጎደለው፣ በአድልኦ የተሞላ፣ የትክክለኛነት ችግር ያለበት፣ ለአንድ አካል የወገነ እንዲሁም የኢትዮጵያ መንግሥትና ህዝብ ክልሉን መልሶ ለመገንባት እያደረጉ ያለውን ጥረት ሙሉ በሙሉ የካደ ዘገባ እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰው ይህም የመረጃ እጥረት እንዳልሆነያመላክታል ነው ያሉት።

እንደ አቶ ወንድወሰን ማብራሪያ ፣የመገናኛ ብዙሃን ባለሥልጣን ከዚህ ቀደም የተዛቡ ዜናዎች እና ዜና ነክ ዘገባዎችን ሲያሰራጩ የነበሩ ጋዜጠኞች ላይ የሥራ ፍቃድ እስከመሰረዝ የደረሰ እርምጃ ወስዷል።

አንዳንድ ወኪሎችን ከሀገር አስወጥቷል ፣በአንዳንዶች ላይ ጥብቅ ማስጠንቀቂያ ፅፎባቸዋል።

የተዛቡ ዘገባዎችን በሚሰሩ ባለሙያዎች ላይ የተወሰዱ እርምጃዎች የመጨረሻ ግብ አይደሉም  ያሉት አቶ ወንድወሰን፤ በቀጣይም የሀገሪቱን ሉዓላዊነት የሚዳፈሩ፣ አብሮነትን የሚፈታተኑ ሥራዎችን የሚሰሩ ሚዲያዎችና ባለሙያዎች ላይ እርምጃዎችን እንደሚወስድ መናገራቸውን ኢፕድ ዘግቧል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.