የሀገር ውስጥ ዜና

የኢትዮ ጂቡቲ የጋራ ድንበር አስተዳዳሪዎች ስብሰባ በጅግጅጋ እየተካሄደ ነው

By Tibebu Kebede

January 14, 2020

አዲስ አበባ፣ ጥር 5፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) 26ኛው የኢትዮጵያ እና ጂቡቲ የጋራ ድንበር አስተዳዳሪዎች ስብሰባ በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ከተማ እየተካሄደ ነው።

የጋራ ድንበር አስተዳዳሪዎች ስብሰባ ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ቀናት የሚካሄድ ይሆናል።

የሶማሌ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ መሃመድን ጨምሮ ሌሎች የሁለቱ ሀገራት የመንግስት የስራ ኃላፊዎች እና የመከላከያ አመራሮች እየተሳተፉ ነው።

ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት የኢትዮ – ጅቡቲ ግንኙነት ከጋራ ድንበር አስተዳደር ባለፈ በደም የተሳሰረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ አልማዝ መኮንን ሃገራቱ ያላቸው የኢኮኖሚ ፣ ማህበራዊ እና ደህንነትን የማስከበር የጋራ ግንኙነት ተጠናክሮ መሄድ እንዳለበት አውስተዋል።

የውይይት መድረኩ የድንበር አስተዳደር፣ የንግድ ግንኙነት እና የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት ማጠናከር ላይ ትኩረቱን በማድረግ ነው በመካሄድ ላይ የሚገኘው።