የሀገር ውስጥ ዜና

የህዳሴ ግድብ ድርድር በአፍሪካ ህብረት ማዕቀፍ እና በሃገራቱ ብቻ መታየት አለበት – የሩሲያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር

By Meseret Awoke

April 13, 2021

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 5፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ) የታላቁ ህዳሴ ግድብ ድርድር በአፍሪካ ህብረትና ማዕቀፍ እና በሶስቱ ሃገራት ብቻ መታየት እንዳለበት የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ አስገንዝበዋል፡፡

ኢትዮጵያ እየገነባችው ባለው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሂደት ላይ የሚስተዋሉ አለመግባባቶች መፈታት ያለባቸው በመነጋገር ብቻ ሊሆን እንደሚገባም ነው ሚኒስትሩ የገለጹት፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከግብጹ አቻቸው ሳሜህ ሽኩሪ ጋር በካይሮ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

በመግለጫቸውም “ልዩነቱ እንዲስተካከል ሩሲያ ጽኑ ፍላጎት እንዳላት ጠቅሰው፥ በተለይ ሶስቱ ሃገራት በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ሩሲያ የቴክኒክ ድጋፍ ታደርጋለች ” ብለዋል፡፡

ልዩነቱ መፈታት ያለበትም በውጭ አካላት ሳይሆን በራሳቸው ሶስቱ ሀገራት ብቻ መሆን እንዳለበት አጽንዖት ሰጥተዋል፡፡

ድርድሩም በአፍሪካ ህብረት ማዕቀፍ እንዲሁም በሶስቱ ሃገራት ብቻ መታየት እንዳለበት ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም ሚኒስትሩ ለድርድሩ ስኬታማነት የሩሲያ አመራሮች እንዲሁም የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ባለሙያዎች በቴክኒክ ጉዳዮች ላይ ድጋፍ ያደርጋሉ ነው ያሉት፡፡

“ሩሲያ የአፍሪካ ሀገራት የራሳቸውን ችግሮች በራሳቸው እንዲፈቱ ታበረታታለች” ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን