የሀገር ውስጥ ዜና

አምባሳደር ነቢል ማህዲ ከደቡብ ሱዳን ምክትል ፕሬዚደንት ጋር ተወያዩ

By Meseret Awoke

April 30, 2021

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 22፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ)በደቡብ ሱዳን የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ነቢል ማህዲ ከደቡብ ሱዳን ምክትል ፕሬዚደንትና የአገሪቱ የመሰረተ ልማት ክላስተር ሰብሳቢ ታባን ደንግ ጋር ተወያይተዋል፡፡

በውይይታቸው ወቅት፤ የመንግስታት መቀያየር ኢትዮጵያ ደቡብ ሱዳንን ከመደገፍ አንጻር የፀና አቋም ያላት መሆኑን አምባሳደሩ ገልጸዋል፡፡

አገራቱ በሰላም ትግበራ፣ መሰረተ ልማት እና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ከማረጋገጥ አኳያ ቀጣይነት እንዳለውም ገልፀዋል፡፡

እንደአምባሳደሩ ገለጻ፤ በትግራይ ከተከናወነው የህግ ማስከበር እርምጃ በኃላ መንግስት 70 በመቶ የሚሆነውን የሰብዓዊ ድጋፍ እያቀረበ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጋር ተያይዞ ከ65 ሚሊየን በላይ ኢትዮጵያውያን የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት እንደሌላቸው አመላክተው፤ ግድቡ ለኃይል ማመንጨት ተግባር የሚውል ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

አምባሳደሩ ግድቡ ለተፋሰሱ አገራት ብዙ ጥቅሞች እንዳሉት ያስረዱ ሲሆን፤ ሱዳንን ከጎርፍ አደጋ የሚታደግ ፕሮጀክት መሆኑንም እንደአብነት አንስተዋል፡፡

በዚህም ግብጽና ሱዳን ኢትዮጵያ የአባይን ውሃ የመጠቀም ሉዓላዊ መብቷን ማክበር እንደሚገባቸውም አሳስበዋል፡፡

የደቡብ ሱዳን ምክትል ፕሬዚደንትና የአገሪቱ የመሰረተ ልማት ክላስተር ሰብሳቢ የሆኑት ታባን ደንግ፤ የሁለቱን አገራት ስር የሰደደ እና የተቆራኘ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በመግለፅ፤ የኢትዮጵያ ሰላም ለደቡብ ሱዳንና ለቀጠናው ሰላም መሆን አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡

በተጨማሪም በትግራይ ሰላም ለማስፈንና ወደ መደበኛ ሁኔታ ለመመለስ እንዲሁም የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት አኳያ መንግስት እያከናወነ ያለውን ተግባር አድንቀው፤ የኢትዮጵያን የውስጥ ጉዳይን ለፖለቲካ ዓላማቸው ማስፈፀሚያ የሚንቀሳቀሱ ኃይሎችን ማውገዛቸውን ከውጭ ጉዳ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጋር ተያይዞም በታዳሽ የኃይል ምንጭነት ለቀጠናው ያለውን ጠቀሜታ ጠቅሰው፤ የዓባይ ወንዝ የሁሉም የተፋሰሱ አገራት የተፈጥሮ ስጦታ በመሆኑ በአግባቡ ከተጠቀሙበት በቂ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም ምክትል ፕሬዚዳንቱ የቀጠናው አገራትን በመንገድ መሰረተ ልማት ማስተሳሰር አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!