የሀገር ውስጥ ዜና

የፖስታ አገልግሎት የዲጂታል ፍኖተ ካርታ ወደ ትግበራ ሊገባ ነው

By Meseret Awoke

May 18, 2021

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 10፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ)የጀርመን መንግስት ድጋፍ ያደረገለት የፖስታ አገልግሎት የዲጂታል ፍኖተ ካርታ ወደ ትግበራ ሊገባ መሆኑ ተገለጸ።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎትና የጀርመን የኢኮኖሚ ጉዳዮችና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኢትዮጵያን ፖስታ አገልግሎት ለማዘመን በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት አድርገዋል።

የፖስታ አገልግሎቱን ለማዘመን የሚያስችል ጥናት ሲደረግ ቆይቶ የተጠናቀቀ ሲሆን፤ በጥናቱ መሰረት የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎትን በዲጂታል መንገድ ለማዘመን የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ ወደ ትግበራ ለመግባት የሚያስችል ውይይት እየተደረገ ነው።

የትግበራው አካል የሆነውን ስምምነት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር አህመዲን መሀመድ፣ የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ስራ አስፈፃሚ ሃና አርያስላሴ እና በጀርመን የኢኮኖሚ ጉዳዮችና ኢነርጂ ሚኒስቴር በኩል በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር ቀዳሚ ፀሃፊ ሆልዝፉስ ካሌ ፈርመውታል።

ሚኒስትር ዴኤታው የጀርመን መንግስት የኢትዮጵያ የፖስታ አገልግሎትን ለማዘመን እያደረገ ላለው ድጋፍ አመስግነዋል።

የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ውስጥ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ የሚደገፉ አገልግሎቶችን መስጠት አንዱ ስራ መሆኑን የገለፁት ሚኒስትር ዴኤታው፤ የፖስታ አገልግሎት ማዘመን ለኢኮሜርስ አገግልግሎት ጅማሮ መደላድል ይፈጥራልም ብለዋል።

የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈፃሚ ወይዘሮ ሃና አረያስላሴ የፖስታ ዲጂታል ፍኖተ ካርታው በፍጥነት ወደ ትግበራ እንዲገባ የጀርመን መንግስት ድጋፉን እንዲያጠናክር መጠየቃቸውን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር ቀዳሚ ፀሃፊ ሆልዝፉስ ካሌ ከፍኖተ ካርታው ትግበራ በተጨማሪ በቀጣይ በተለያ ጉዳዮች በጋራ እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!