የሀገር ውስጥ ዜና

መገናኛ ብዙኃን ለሰላም፣ ለአብሮነት፣ ለዴሞክራሲና ለሀገር ግንባታ ሊሰሩ እንደሚገባ ተገለፀ

By Feven Bishaw

May 20, 2021

አዲስ አበባ ፣ ግንቦት 12፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን “መገናኛ ብዙኃን ለሰላም፣ ለአብሮነትና ለሀገር ግንባታ” በሚል ውይይት አካሂዷል።

በውይይቱ የሰላም ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን የቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሮ ሙፈሪሃት ካሚል ሚዲያው ባለፋት ጊዜያት ግልጽ በሆነ ፖሊሲ ሳይመራ በመቆየቱ ማደግ የሚገባውን ያክል ማደግ ሳይችል ቀርቷል ብለዋል።

ከለውጡ በኋላ መንግስት ለዴሞክራሲ ግንባታ ትልቅ አቅም አላቸው ብሎ ከለያቸው ሴክተሮች አንዱ ሚዲያው መሆኑንም አንስተዋል፡፡

በመሆኑም አዳዲስ ስትራቴጂዎችና ፖሊሲዎች ተቀርጸው የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣንን ሚና ለመቀየር ተሞክሯል ያሉት ሚኒስትሯ አሁን በፊት ከነበረው የተቆጣጣሪነት መንፈስ በመውጣት የማስቻል ስራ እንዲሰራ መደረጉንም ጠቅሰዋል።

በዚህም አሁን ሚዲያዎች ለሰላም ለዴሞክራሲና ለሀገር ግንባታ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ የማስቻል ስራዎችንም ይሰራል ነው ያሉት፡፡

የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መሀመድ ኢድሪስ በበኩላቸው ሚዲያ ድምጽ ለሌላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ድምጽ በመሆን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ስብራቶችን በመጠገን የተጀመረውን ሪፎርም ለማስቀጠል እንደሚሰሩ እምነታቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በዘመን በየነ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!